Mols.gov.et

mols mols

News

በመጀመሪያው ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ውድድር ኢትዮጵያውያኑ የፈጠራ ባለሙያዎች ከፍተኛ ውጤ

በመጀመሪያው ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ውድድር ኢትዮጵያውያኑ የፈጠራ ባለሙያዎች ከፍተኛ ውጤት አስመዘገቡ
በፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት ከአጋር ተቋማት ጋር በመተባበር በተዘጋጀው የመጀመሪያው ዓለም አቀፍ የቴክኒክና ሙያ የጥናትና ምርምር ጉባኤ እና የቴክኖሎጂ ውድድር፣ ኢትዮጵያውያኑ የፈጠራ ባለሙያዎች አንደኛና ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ውድድሩን አጠናቀዋል።
ከሰኔ 5 ጀምሮ ለሦስት ተከታታይ ቀናት በተካሄደው በዚህ መድረክ ከ10 አገራት የቀረቡ 35 የፈጠራ ሥራዎች ውስጥ 6ቱ ለፍጻሜ የደረሱ ሲሆን፣ 4ቱ ከኢትዮጵያ፣ 1 ከሕንድ እና 1 ከናይጄሪያ ነበሩ።
በመጨረሻው ውድድር የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም ግብርናን ለማጎልበት የሚያስችል በIoT ቴክኖሎጂ የተደገፈ ዘመናዊ የመስኖ ክትትልና ቁጥጥር ሥርዓት ያቀረበው ዘላለም እንዳለው አንደኛ ደረጃን በመያዝ የዋንጫና የወርቅ ሜዳሊያ ተሸላሚ ሆኗል።
አካልን ሳይጎዳ የጭንቅላት ውስጥ ግፊትን ለመለካት የሚያስችል CEREBRO-LOGIC የተሰኘ ፈጠራ ያቀረቡት ሩት ጌታቸው፣ ሀመረ፣ ያብስራ እና ሪሀና ሁለተኛ ደረጃን በማግኘት የብር ሜዳሊያ ተሸላሚ ሆነዋል።
ከናይጄሪያ የቀረበው የገቢ መረጃና ተከታታይነት ማረጋገጫ ሥርዓት (Revenue Intelligence and Traceability System) ደግሞ ሦስተኛ ደረጃን በማግኘት የነሐስ ሜዳሊያ ተሸላሚ ሆኗል።
የፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ብሩክ ከድር ለአሸናፊዎቹ እንኳን ደስ አላችሁ በማለት፣ ውጤቱ የኢትዮጵያ ወጣቶች በምርምር፣ በክህሎትና በፈጠራ ያላቸውን አቅም በግልጽ ያሳየ መሆኑን ገልጸዋል።
የፈጠራ ሥራዎቹ ከውድድር ባሻገር ወደ ሥራ እና ወደ ገበያ እንዲገቡ አስፈላጊ ድጋፎች ሊጠናከሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።
በማጠቃለያው ሥነ ሥርዓት ላይ ለሁሉም ተወዳዳሪዎች የምስክር ወረቀት የተበረከተ ሲሆን፣ ለአሸናፊዎችም እንደየደረጃቸው ሜዳሊያና ልዩ ሽልማቶች ተሰጥተዋል።

Read More »
News

ምርምር፣ ፈጠራና አጋርነት የዘላቂ የኢንዱስትሪ ሽግግር መሠረቶች ናቸው ዶ/ር ብሩክ ከድር

ምርምር፣ ፈጠራና አጋርነት የዘላቂ የኢንዱስትሪ ሽግግር መሠረቶች ናቸው
ዶ/ር ብሩክ ከድር
የፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር
በፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት አዘጋጅነት ሲካሄድ የነበው የመጀመሪያው ዓለም አቀፍ የቴክኒክና ሙያ ምርምር ኮንፈረንስና የቴክኖሎጂ ውድድር በስኬት ተጠናቋል።
መድረኩ ከ16 በላይ ሃገራት ተወዳዳሪዎች፣ የኢንዱስትሪ ባለሙያዎች፣ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ተቋማት፣ የልማት አጋሮችና የዘርፉ ተዋናዮችን በአንድ ያገናኘ ነው።
የፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ክቡር ዶ/ር ብሩክ ከድር በመዝጊያ መርሃ ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ምርምር፣ ፈጠራና አጋርነት የዘላቂ የኢንዱስትሪ ሽግግር መሠረቶች ናቸው ብለዋል፡፡
የመጪውን ዘመን ፍላጎት የሚመለስ የክህሎት ልማት ስርዓት ለመገንባት የምርምር ባህልን ማጠናከር፣ ፈጠራን ማበረታታት እና ከኢንዱስትሪ፣ ከዩኒቨርሲቲዎችና ከዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር ያለውን ትብብር ማስፋት ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል።
በኮንፈረንሱ 85 የምርምር ጽሑፎች ቀርበው 31 ጥራት ያላቸው ጥናቶች ለመድረክ የተመረጡ ሲሆን፣ 29 የምርምር ሥራዎች በዲጂታል ሽግግር፣ በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI)፣ በኢንዱስትሪ 4.0፣ በአረንጓዴ ክህሎቶች፣ በታዳሽ ኃይል እና በአካታች የቴክኒክና ሙያ ሥርዓት ግንባታ ዙሪያ ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።
በቴክኖሎጂ ውድድሩ ከ10 አገራት የተውጣጡ 35 ፈጠራዎች የቀረቡ ሲሆን፣ ኢትዮጵያውያን ወጣት የፈጠራ ባለሙያዎች አንደኛና ሁለተኛ ደረጃዎችን በመያዝ እንደ ሃገር ያለንን የፈጠራ አቅም አሳይተዋል።
በቴክኖሎጂ ውድድሩ የIoT Smart Irrigation System አንደኛ ደረጃን ሲያገኝ፣ የCerebro Logic ሁለተኛ ደረጃን አግኝቷል። የናይጄሪያው Eco-Bin Revenue Intelligence and Traceability System ደግሞ ሦስተኛ ደረጃን በማግኘት የነሃስ ሜዳሊያ ተሸልሟል።
በመድረኩ በአንጎል ውስጥ ግፊትን ያለ ቀዶ ሕክምና ለመለካት የሚችለውን Cerebro Logic የተሰኘ ቴክኖሎጂን የሰሩት ወጣት ሴት የፈጠራ ባለሙያዎች ልዩ አድናቆት ተችሯቸዋል፡፡
የቀረቡት ጥናቶችና ፈጠራዎች በወረቀት ላይ ብቻ ሳይቀሩ ወደ ተግባርና ወደ ገበያ እንዲሸጋገሩ የፈጠራ ማበልጸጊያ ማዕከላት፣ የቴክኖሎጂ ሽግግር ሥርዓቶች እና የምርምር ትብብሮች የበለጠ መጠናከር እንዳለባቸው ዶ/ር ብሩክ አሳስበዋል።

Read More »
News

በ27 ከተሞች ከ1መቶ ሺ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ …

በ27 ከተሞች ከ1መቶ ሺ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል የፕሮግራም ማሻሻያ ይፋ ሆነ
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከዓለም ባንክ ጋር በመተባበር የወጣቶች የሥራ ልምምድ ፕሮግራም በሆነው «ብቃት» እና «የሥራ ማዕከላት አገልግሎት ማሻሻያ » ፕሮግራሞችን በአዳዲስ ከተሞች ለማስፋት የሚያስችል የማብሰሪያ መድረክ አካሂዷል፡፡
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የሥራ፣ የሥራ ሥምሪትና ገበያ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር አቶ ሰለሞን ሶካ በመድረኩ ላይ እንደገለፁት፣ ከ18-25 የሆኑና የትምህርት ደረጃቸው 12ኛ ክፍልና ከዚያ በታች የሆኑ ሥራ ፈላጊ ወጣቶችን ሕይወት በመለወጥ ረገድ የ«ብቃት» ፕሮግራም ከፍተኛ ስኬት አስመዝግቧል፡፡
እስካሁን 93 ሺህ 665 የሚሆኑ ወጣቶች የሕይወት ክህሎት ሥልጠና ያገኙ ሲሆን 54 ሺህ 913 ወጣቶች ደግሞ የስድስት ወር የተግባር ልምምዳቸውን አጠናቀዋል፡፡
ከእነዚህም ውስጥ 52 ሺህ 786 የሚሆኑት ቋሚ የሥራ ዕድል ተፈጥሮላቸዋል፡፡
ከተጠቃሚዎቹ መካከልም 67.6 በመቶ ያህሉ ወጣት ሴቶች መሆናቸው ፕሮግራሙ ማኅበራዊ ፍትሐዊነትን በግልፅ ያመላከተ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡
በሌላ በኩል “የሥራ ማዕከላት አገልግሎት ማሻሻያ” ፕሮግራም ባለፉት ዓመታት በአምስት ክልሎችና በሁለት ከተማ አስተዳደሮች የሚገኙ 18 የሥራ ማዕከላት ዕድሳት ተደርጎላቸው የቢሮ መገልገያ ቁሳቁስ የተሟላላቸው ሲሆን አገልግሎታቸውንም ከኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት ጋር የማቀናጀት ሰፊ ሥራ ተከናውኗል፡፡
ከዓለም ባንክ በተገኘ የ52 ሚሊዮን ዶላር ተጨማሪ ፋይናንስ የ«ብቃት» ፕሮግራም ተጠቃሚ ከተሞች ቁጥር ከ11 ወደ 27 ለማስደግ መቻሉን፣ ብሎም በሚቀጥሉት 2 ዓመታት ውስጥም ዕድሜያቸው ከ18 እስከ 29 የሆኑ 100,000 አዳዲስ ወጣቶች ተጠቃሚ እምደሚሆኑ ክቡር ሚኒስትር ዴኤታው ይፋ አድርገዋል፡፡
ወደ ፕሮግራሙ አዲስ ከሚገቡት 16 ከተሞች መካከል ሰበታ፣ ቡራዩ፣ ቢሾፍቱ፣ አሰላ፣ አምቦ፣ ነቀምት፣ አርባ ምንጭ፣ ሆሳዕና፣ ዲላ፣ ደሴ፣ ደብረ ማርቆስ፣ ደብረ ታቦር፣ ደብረ ብርሃን፣ ሽሬ እንዳሥላሴ፣ ጅጅጋ እና ሐረር እንደሚገኙበት ተገልጿል፡፡
በሌላ በኩል በ«የሥራ ማዕከላት አገልግሎት ማሻሻያ»ፕሮግራም አማካኝነት በሁሉም ክልሎች በሚገኙ 88 የምግብ ዋስትና ፕሮጀክት በሚተገበርባቸው ከተሞች ውስጥ ተጨማሪ 200 የሥራ ማዕከላት የአቅም ግንባታ ድጋፍ ያገኛሉ።
እነዚህ ማዕከላት የቢሮ መገልገያ መሣሪያዎች ተሟልተውላቸው አገልግሎታቸው ሙሉ በሙሉ ዲጂታላይዝድ የሚደረግ ሲሆን የኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓትንም ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንደሚያደርጉም ተመላክቷል፤
አዳዲስ ወደ ፕሮግራሙ የሚገቡ ከተሞች ከነባሮቹ ተሞክሮ በመውሰድ የተሻለ ውጤት እንዲያስመዘግቡ ፤ እንዲሁም በየደረጃው የሚገኙ የዘርፉ አመራሮች፣ ከንቲባዎችና ባለድርሻ አካላት ለፕሮግራሞቹ ውጤታማነት ከወዲሁ ዝግጅት እንዲያደርጉ ክቡር አቶ ሰለሞን ሶካ የሥራ መመሪያ ሰጥተዋል፡፡

Read More »
News

ለኢትዮጵያ ስታርትአፖች የዓለም አቀፍ ፋይናንስና የገበያ ዕድሎችን…

ለኢትዮጵያ ስታርትአፖች የዓለም አቀፍ ፋይናንስና የገበያ ዕድሎችን የሚያሰፋ የአጋርነት ስምምነት
የኢንተርፕረነርሺፕ ልማት ኢንስቲትዩት (EDI) በአገር ውስጥ ያሉ ስታርትአፖችን፣ አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችን እንዲሁም በፈጠራ ላይ የተመሰረቱ የንግድ ተቋማትን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ለማድረግ የሚያስችል ስትራቴጂካዊ የአጋርነት ስምምነት በኖርዌይ መቀመጫነቱን ካደረገው ዩሮኖርዲክ ፈንዲንግ አሊያንስ (ENFA) ጋር ተፈራረመ።

ይህ አጋርነት በኢትዮጵያ ውስጥ እየተገነባ ያለውን የሥራ ፈጠራና የስታርትአፕ ሥነ-ምህዳር ይበልጥ ለማጠናከር ታስቦ የተዘጋጀ ሲሆን፤ ለአገር ውስጥ ሥራ ፈጣሪዎች አዳዲስ ዓለም አቀፍ የፋይናንስ፣ የቴክኖሎጂና የገበያ በሮችን የሚከፍት መሆኑ ተገልጿል።

‎በሁለቱ ተቋማት መካከል የተደረገው ስምምነት የአገር ውስጥ ስታርትአፖች በቀላሉ የዓለም አቀፍ የገንዘብ ድጋፎችን፣ የተቀላቀሉ ፋይናንሶችን (Blended Finance) እና የግል ኢንቨስትመንቶችን እንዲያገኙ ምቹ ሁኔታዎችን ይፈጥራል።

በተጨማሪም የኢትዮጵያ ስታርትአፖች አቅማቸውን በማሳደግ ምርትና አገልግሎታቸውን ወደ ዓለም አቀፍ ገበያ በተለይም ወደ አውሮፓ፣ ወደ ኖርዲክ አገራት፣ እንዲሁም በመካከለኛው ምስራቅና ሰሜን አፍሪካ (MENA) ቀጠናዎች እንዲያስፋፉ ስትራቴጂካዊ ድጋፍ ይደረግላቸዋል።
‎ትብብሩ የሥራ ፈጣሪዎችን አቅም ለመገንባት የሚያግዙ ልዩ ሥልጠናዎችንና የምክር (Coaching) አገልግሎቶችን የሚያካትት ሲሆን፣ አገር በቀል ፈጠራዎች በዓለም አቀፍ ጥምረቶች ውስጥ እንዲሳተፉ ዕድል ይፈጥራል።
‎በዚህ ስምምነት መሠረት የኢትዮጵያ ስታርትአፖች እና የስነ-ምህዳሩ አንቀሳቃሾች የዩሮኖርዲክ ፈንዲንግ አሊያንስ (ENFA) የሚያቀርባቸውን ዘመናዊ ዲጂታል አገልግሎቶች በይፋ ማግኘት የሚችሉ ይሆናል።


‎ በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) የታገዙ የእርዳታና ፋይናንስ መፈለጊያ መሣሪያዎች፣ዓለም አቀፍ የኔትወርክና የትስስር መድረኮች፣የዓለም አቀፍ ፕሮጀክትና የገንዘብ መጠየቂያ ፕሮፖዛል ዝግጅት ድጋፎች፣ እንዲሁም
‎ከውጭ ኢንቨስተሮች ጋር በቀጥታ የሚያገናኙ የኢንቨስትመንት ትስስር (Matchmaking) ዕድሎች ከአገልግሎቶቹ መካከል ተጠቃሽ ናቸው፡፡

የተቋማቱ ተወካዮች በፊርማ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንደገለጹት፣ በኢትዮጵያ ውስጥ የሥራ ፈጠራና የቴክኖሎጂ አድማስን ለማስፋት ዓለም አቀፍ ትብብር ማድረጉ አማራጭ የሌለው ጉዳይ ነው። ይህ ተነሳሽነት የአገር ውስጥ ሥራ ፈጣሪዎች አስፈላጊውን ስትራቴጂካዊ ሀብትና ዕውቀት አግኝተው በዓለም መድረክ ላይ ብቁ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ በቀጥታ ያግዛል።
ዩሮኖርዲክ ፈንዲንግ አሊያንስ (ENFA) ከ20 በላይ አገራት ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የተለያዩ የፋይናንስ ድርጅቶችን፣ የባለሙያ ተቋማትን እና የፈጠራ አጋሮችን በአንድ ላይ ያቀፈ ትልቅ ዓለም አቀፍ ጥምረት ሲሆን፤ ይህ ስምምነት የኢንተርፕረነርሺፕ ልማት ኢንስቲትዩት (EDI) በኢትዮጵያ ውስጥ ተንቀሳቃሽ፣ ዘመናዊ እና በዓለም አቀፍ ደረጃ የተገናኘ የኢንተርፕረነርሺፕ ሥነ-ምህዳር ለመገንባት የያዘውን አገራዊ ራዕይ የሚያፋጥን መሆኑ ታውቋል።
ዘገባው የኢንተርፕሪነርሺፕ ልማት ኢኒስቲትዩት ነው;

Read More »
News

ኢንስቲትዩቱ ታላቅ ዓለም አቀፍ የምርምር ጉባኤና የቴክኖሎጂ ውድድር ሊያካሂድ ነው

ኢንስቲትዩቱ ታላቅ ዓለም አቀፍ የምርምር ጉባኤና የቴክኖሎጂ ውድድር ሊያካሂድ ነው
የፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት (FDRE TVTI) ከሰኔ 5 እስከ 7 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ለተከታታይ ሦስት ቀናት የሚቆይ ታላቅ ዓለም አቀፍ የምርምር ጉባኤ እና የቴክኖሎጂ ውድድር እንደሚያካሂድ አስታወቀ።
የኢንስቲትዩቱ የጥናትና ምርምር ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ሀብታሙ ሙሉጌታ ዛሬ ለተለያዩ ሚዲያ አካላት በሰጡት ጋዜጣዊ
የዓለም አቀፍ ኮንፈረንሱ ዋና ዓላማ በኢኒስቲትውቱ የምርምርና ቴክኖሎጂ ስራዎችን ዓለም አቀፋዊ ተወዳዳሪነት ማሳደግ፣ የልምድ ልውውጥ ማካሄድ፣ እንዲሁም በተመራማሪዎች፣ ፖሊሲ አውጪዎች፣ የኢንዱስትሪ መሪዎችና የልማት አጋሮች መካከል ያለውን ቅንጅትና አጋርነት ማጠናከር ነው።
ዘንድሮ የሚካሄደው ይህ ታላቅ ጉባኤ፦ “Future-Ready TVET and Technological Innovation for Sustainable Industrial Transformation” ወይም “መጻኢ የክህሎት ልማትና ቴክኖሎጂያዊ ፈጠራን ያቀፈ ዘላቂ የኢንዱስትሪ ሽግግር” በሚል መሪ ሐሳብ እንዳለው ተገልጿል፡፡
ኮንፍረንሱ በዲጂታል ሽግግር እና የቴቬት ፈጠራኢንዱስትሪያል ለውጥ፣ በፈጠራ እና አረንጓዴ ሥርዓቶች፣በፖሊሲና አስተዳደር አካታችነት እና ዓለም አቀፍ አጋርነት ላይ አተኩሮ እንደሚካሄድም ተጠቁሟል፡፡
በውድድሩ ላይ የሚቀርቡት የቴክኖሎጂ ስራዎችም በICT እና ዲጂታል ፈጠራ (AI, IoT, Cybersecurity)፣ በግብርናና አግሮ-ፕሮሰሲንግ፣ በላቀ ማኑፋክቸሪንግ፣ በታዳሽ ኃይልና አረንጓዴ ቴክኖሎጂ፣ እንዲሁም በግንባታና ዝቅተኛ ወጪ መኖሪያ ቤቶች ዘርፍ የተከፋፈሉ መሆናቸው ተገልጿል።
ላፉት ስድስት ወራት በተጠናከረ ሁኔታ ዝግጅት ሲደረግበት የቆየው ይህ ኮንፈረንስ እጅግ ሰፊ ዓለም አቀፋዊ ይዘት ያለው ሲሆን፤ ከኢትዮጵያ በተጨማሪ ከጀርመን፣ ህንድ፣ ቻይና፣ ናይጄሪያ፣ ሩዋንዳ፣ ኬንያ፣ ቱርክ፣ ኢራን፣ ማላዊ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እና ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ጨምሮ ከ16 አገራት የተውጣጡ ተመራማሪዎችና ተወዳዳሪዎች ይሳተፉበታል።
በጉባኤው ላይ ከ90 በላይ የምርምር ጽሑፎች እና ከ100 በላይ የቴክኖሎጂ/ፈጠራ ፕሮጀክቶች ከተመራማሪዎችና ባለሙያዎች የቀረቡ ሲሆን፤ በጥብቅ የሳይንሳዊ ግምገማ ሂደት ያለፉ 30 ከፍተኛ ጥራት ያላቸው የምርምር ጽሑፎች እና 34 የተመረጡ የቴክኖሎጂ ስራዎች ለቀራቢነትና ለውድድር በብቃት ማለፋቸውን ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል።
በኮንፈረንሱ ላይ ኢንዱስትሪዎች፣ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት፣ የቴክኒክና ሙያ ተቋማት፣ የመንግስት ተቋማት፣ የልማት አጋሮች፣ ተመራማሪዎች፣ የፈጠራ ባለቤቶች እና ፖሊሲ አውጪዎች በጋራ ይሳተፋሉ።

Read More »
News

የትምህርት ሥርዓትን ከገበያ ፍላጎት ጋር ማጣጣም

የትምህርት ሥርዓትን ከገበያ ፍላጎት ጋር ማጣጣም ዘላቂ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ወሳኝ ነው
የትምህርት ሥርዓትን ከገበያ ፍላጎት ጋር ማጣጣም ዘላቂ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ወሳኝ መሆኑን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ምክትል ዋና ጸሀፊ አሚና መሐመድ ገለጹ።
በሥራ ፈጠራ ላይ ትኩረቱን ያደረገ የአፍሪካ ዴቨሎፕመንት ኢምፓክት ፎረም 2026 በተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ECA) መካሄድ ጀምሯል።
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ምክትል ዋና ጸሀፊ አሚና መሐመድ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ አፍሪካ ታላላቅ ተግዳሮቶችና መልካም አጋጣሚዎች ባሉበት ወሳኝ መስቀለኛ መንገድ ላይ ትገኛለች፡፡
በዚህ ወቅት ጥራትና ዘላቂነት ያላቸው የሥራ ዕድሎችን ለመፍጠር ዘመናዊ የትምህርት ሥርዓቶችን ከገበያው ትክክለኛ ፍላጎት ጋር ማጣጣም እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በተለይም በፍጥነት እያደገ የመጣውን የአፍሪካ ወጣት ቁጥር ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ጥራት ያላቸው የሥራ ዕድሎችን መፍጠር አፋጣኝ ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ሊሆን እንደሚገባ አሳስበዋል።
ባለፉት ዓመታት ከአምራች ኢንዱስትሪ መስፋፋት እስከ ወጣቶች የሥራ ዕድል ፈጠራና የክህሎት ልማት ያሉ የአፍሪካን አንገብጋቢ ተግዳሮቶች ለመፍታት ከመንግሥታት፣ ከቀጣናዊ ተቋማትና ከግል ዘርፉ ጋር በጋራ ሲሠራ መቆየቱን አስታውሰዋል።
ከዚህ የጋራ ሥራም ትልቅ ትምህርት መገኘቱን ጠቅሰው፣ምርምር፣መረጃና ማስረጃዎች ብቻቸውን ለውጥ አያመጡም፤ ከንግግርና ከሪፖርት ባለፈም ወደ ተግባራዊ እርምጃ መግባት አማራጭ የሌለው ጉዳይ ነው ብለዋል።
የስራ ዕድሎችን መፍጠር በመንግሥታት ብቻ ሊሳካ እንደማይችል ጠቁመው፤ይህም የፖሊሲ አውጪዎችን፣ ተመራማሪዎችን፣ የልማት አጋሮችንና የግል ዘርፉን በአንድ ላይ የሚያገናኝ ንቁ ሥነ-ምሕዳርን እንደሚጠይቅ አስረድተዋል።
የዘንድሮው ፎረም መፍትሔዎችን ለመለየት፣ጠንካራ አጋርነትን ለመገንባትና ተግባራዊ የመድረሻ መንገዶችን ለመንደፍ የተለያዩ ባለድርሻ አካላትን በአንድ ላይ ያገናኘ ሲሆን፣ከውይይት ባለፈ በመላው አፍሪካ ላሉ ወጣቶች ወደ ተጨባጭ ውጤት የሚቀይሩ ትርጉም ያላቸው ተግባራት እንደሚጠበቁበት ተመላክቷል። መረጃው የኢዜአ ነው። See less

Read More »
News

ከ218 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነባው የማዕክ-ዱግሲየ የክህሎትና የእደ-ጥበብ ኮሌጅ

ከ218 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነባው የማዕክ-ዱግሲየ የክህሎትና የእደ-ጥበብ ኮሌጅ ተመረቀ
በሶማሌ ክልላዊ መንግሥት ,በአውባሬ ከተማ ከ218 ሚሊዮን የኢትዮጵያ ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባው የማዕክ-ዱግሲየ የክህሎትና የእደ-ጥበብ ኮሌጅ በዛሬው ዕለት በይፋ ተመርቋል።
ሪቫን በመቁረጥ ኮሌጁን በይፋ ያስመረቁት የሶማሌ ክልል ፕሬዝዳንት አቶ ሙስጠፌ ሙሐመድ ዑመር እና የሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሁሴን ጋይድ ናቸው።
ይህ ግዙፍ የክህሎት ማሰልጠኛ ተቋም በ(25ሺ ካሬ ሜትር መሬት ላይ ያረፈ ሲሆን፥ በውስጡም 21 የተለያዩ የሕንጻ ብሎኮችን አካቷል። ኮሌጁ በተለያዩ የሙያና የቴክኒክ ዘርፎች በየዓመቱ ለ1,500 ሰልጣኞች ጥራት ያለው ትምህርትና ስልጠና ለመስጠት የሚያስችል አቅም እንዳለው ተገልጿል።
ተቋሙ የተሟላ የትምህርትና የማሰልጠኛ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉ እንደ የተማሪዎች መኝታና የመመገቢያ አዳራሾች፣ የመማሪያ ክፍሎች፣ የተግባር ልምምድ ማድረጊያ ማዕከላት (ወርክሾፖች)፣ የአስተዳደር ቢሮዎችና አጠቃላይ አገልግሎት መስጫዎችን በውስጡ ይዟል።
ከዚህ በተጨማሪም የዚህ መሰል ከፍተኛ ኮሌጆችን ደረጃ የጠበቁ የተማሪዎች መዝናኛ ስፍራዎችና የስፖርት ማጫወቻ ሜዳዎች ተካተውለታል።
በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ማጠቃለያ ላይ የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በኮሌጁ ቅጥር ግቢ ውስጥ የችግኝ ተከላ መርሐ-ግብር አከናውነዋል።

Read More »
News

ሉሲ ገበያ- የኢንተርፕራይዞችን የገበያ ምህዳር የማስፋት ጅምር

ሉሲ ገበያ- የኢንተርፕራይዞችን የገበያ ምህዳር የማስፋት ጅምር
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የአገር በቀል ኢንተርፕራይዞችን የንግድ ተወዳዳሪነት ለማረጋገጥና የገበያ መሰረተ ልማትን ለማስፋት፣ በኢትዮጵያ ሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት በኩል ያበለጸገው «ሉሲ ዲጂታል ገበያ» (Lucy Digital Market) ወደ ሥራ መግባቱ ይታወቃል።
ይህንን ስትራቴጂካዊ ዕቅድ ወደ መሬት ለማውረድና የፕላትፎርሙን አጠቃቀም ለማስፋፋት፣ በአዲስ አበባ ከተማ የሥራና ክህሎት ቢሮ አማካኝነት ከ119 ወረዳዎች ለተውጣጡ የገበያ እና ፕሮሞሽን ባለሙያዎች እና ከ15 የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ለተመረጡ ሰልጣኞች እየተሰጠ ያለው ስልጠና ተጠናክሮ ቀጥሏል።
ስልጠናው በዋናነት በኢ-ኮሜርስ (e-Commerce)፣ በሶሻል ሚዲያ ማርኬቲንግ፣ በዲጂታል ኮሙዩኒኬሽን እና የሉሲ ፕላትፎርም አጠቃቀም በመሳሰሉ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ አተኩሮ እየተሰጠ ይገኛል።
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የገበያ ጥናትና ትስስር ዴስክ ኃላፊ አቶ ሰለሞን ታደሰ በመድረኩ እንደገለጹት ስልጠናው ሲጠናቀቅ እያንዳንዱ ባለሙያ ቢያንስ የ20 ኢንተርፕራይዞችን ምርትና አገልግሎት ወደ ስራ በማስገባት፣ በቀጣይ 3 ወራት በአጠቃላይ ከ3 ሺህ በላይ ኢንተርፕራይዞችን ወደ ዲጂታል የገበያ ትስስሩ ለማስገባት ግብ ተቀምጧል።
አክለውም ይህ ንቅናቄ ኢንተርፕራይዞችን ወደ ዘመናዊው የዲጂታል ዓለም ለማሻገር እና የገበያ ተደራሽነታቸውን ለማፋጠን ከፍተኛ ሚና እንደሚጫወት ገልጸዋል።

Read More »
News

ጠንካራ የሙያ ብቃት ምዘና ሥርዓት፣ ብቁና ተወዳዳሪ ዜጋ፤ ጠንካራ ሀገር!

ጠንካራ የሙያ ብቃት ምዘና ሥርዓት፣ ብቁና ተወዳዳሪ ዜጋ፤ ጠንካራ ሀገር!
የክህሎት ልማት ዘርፋችን ብቁና ተወዳዳሪ ዜጎችን የማፍራት ሀገራዊ ተልዕኮውን በስኬት እንዲወጣ የሙያ ብቃት ምዘና ሚና የማይተካ ድርሻ አለው፡፡
የሙያ ብቃት ምዘናና ማረጋገጫ ሥርዓታችን ተራ የፈተና ሂደት አይደለም፡፡ ይልቁንም ክፍተትን ለይቶ መሙላት እንዲቻልና የዜጎችን ክህሎት ወደ ላቀ ምርታማነት፣ ምርታማነትን ደግሞ ወደ ሀገራዊ እድገት የሚቀይር የሰው ሀብት ልማታችን ዋነኛ የጥራት ማረጋገጫ መሣሪያ ነው!
ይህንን ሀገራዊ ሥርዓት ይበልጥ ዘመናዊ፣ ተደራሽ እና ቀልጣፋ ለማድረግ ከኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት ጋር ሙሉ በሙሉ የማስተሳሰር እና የዲጂታላይዝ የማድረግ ሥራ ተጠናቋል። በዚህም፦
⚡ የምዘናና የብቃት ማረጋገጫ ሂደቱ ፈጣን፣ ቀልጣፋና ምቹ እንዲሆን እና
🛡️ በዘርፉ ይስተዋሉ የነበሩ የአሠራር ክፍተቶችን እና ብልሹ አሠራሮችን ከመሠረቱ የሚቀይር ግልጽ ሥርዓት ለመፍጠር ያስችላል።
ይህንን ሁሉን አቀፍና ደረጃውን የጠበቀ ሥርዓት በመላው ሀገሪቱ ለማስፈን አስቻይና ሰፊ መዋቅር በየደረጃው አለ። በእስካሁኑ ሂደትም፦
🏢 14 የክልልና ከተማ አስተዳደር የሙያ ብቃት ምዘና ኤጀንሲዎች/ባለሥልጣናት፣
🎯 1,843 የምዘና ማዕከላት በመላው ሀገሪቱ አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛሉ።
እነዚህ 14 የክልልና ከተማ አስተዳደር መዋቅሮቻችን ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት እንዲሰጡ ለማስቻል፣ ወደ ዓለም አቀፉ የጥራት ሥራ አመራር ሥርዓት (Quality Management System – ISO) እንዲገቡ የማድረግ ሰፊ ሥራም እየተከናወነ ይገኛል።
በዚህ ቀጣይነት ባለው ጥረት እስካሁን ሚኒስቴር መሥሪያ ቤታችንን እና ተጠሪ ተቋሞቻችንን ጨምሮ በዘርፋችን የዓለም አቀፉን የጥራት ሥራ አመራር ሥርዓት እውቅና ያገኙ ተቋማት ቁጥር ከ20 በላይ ደርሷል።

Read More »
News

«ሉሲ ገበያ»፦ ለኢንተርፕራይዞች ዲጂታል ሽግግር…

«ሉሲ ገበያ»፦ ለኢንተርፕራይዞች ዲጂታል ሽግግር
በዚህ እጅግ ፈጣን የቴክኖሎጂ ዘመን የንግድ ተወዳዳሪነትን ለማረጋገጥ ዲጂታል ስርዓቶች መጠቀም ምርጫ ሳይሆን የግድ ነው።
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከኤስ ኤን ቪ ሊዌ ፕሮግራምና ከአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ በመተባበር የኢንተርፕራይዞችን አቅም ለመገንባትና ምርቶቻቸውን ወደ «ሉሲ ዲጂታል ገበያ» ለማስገባት ለባለሙያዎች እየሰጠ ያለው ስልጠና ለዚህ ትልቅ ማረጋገጫ ነው።
በዚህ የዲጂታል ሽግግር ውስጥ ኢንተርፕራይዞች ምርትና አገልግሎታቸውን በገበያ ላይ ስኬታማ ለማድረግ ብራንዲንግ (Branding) እና ድጅታል ማስታወቂያ መጠቀም ወሳኝ ነው፡፡
ጠንካራ ብራንድ የገነቡ ኢንተርፕራይዞች በደንበኞች ዘንድ ከፍተኛ እምነት ያተርፋሉ፤ ይህም ደንበኛው ያለ ምንም ማንገራገር ምርቱን እንዲሸምት ያደርጋቸዋል።
የ«ሉሲ» የዲጂታል ገበያ ደግሞ ለኢንተርፕራይዞች ተራ የገበያ ቦታ ሳይሆን፣ ምርትና አገልግሎታቸውን በዘመናዊ መንገድ የሚያስተዋዉቁበትና ተጠቃሚነታቸውን ይበልጥ የሚያሳድጉበት ግዙፍ አማራጭ ነው፡፡
ይህ ፕላትፎርም ኢንተርፕራይዞች ከአካባቢያዊ ገበያ ወጥተው በመላው አገሪቱ አልፎም በዓለም አቀፍ ደረጃ ምርቶቻቸውን 24/7 (በየትኛውም ሰዓት) እንዲያስተዋውቁና እንዲሸጡ ዕድል ይፈጥራል።
በሉሲ ፕላትፎርም ላይ የሚደረግ የብራንዲንግና ማስታወቂያ ሥራም ባህላዊ ማስታወቂያዎች (እንደ ቢልቦርድና ጋዜጣ) ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቁትን በማስቀረት በቀጥታ ምርትና አገልግሎት ወደ ፈላጊው ደንበኛ ዘንድ የሚያደርስ መንገድ ነው።
ከሁሉ በላይ አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ሳይቀሩ እንደ ትላልቅ ኩባንያዎች ሁሉ ምርታቸውን በሚያምር አቀራረብ (Professional Packaging & Digital Display) ለገበያ እንዲያቀርቡ ከማስቻል ባሻገር ከደንበኞቻቸው ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት በመፍጠር አስተያየቶችን በፍጥነት እንዲቀበሉና አገልግሎታቸውን እንዲያሻሽሉ ይረዳል።
በአዲስ አበባ ከተማ ሥራና ክህሎት ቢሮ ስር ለሚገኙ የማርኬቲንግ እና ፕሮሞሽን ባለሙያዎችን በኢ-ኮሜርስ፣ ሶሻል ሚዲያ ማርኬቲንግ እና በሉሲ ፕላትፎርም አጠቃቀም ላይ እየተሰጠ ያለው ስልጠና ሲጠናቀቅ በአጭር ጊዜው በሺዎች የሚቆጠሩ ኢንተርፕራይዞች ፕላትፎርሙን ይቀላቀላሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

Read More »
The Minister Is answering questions live in zoomClick To join the live Meeting
+
tigTIG
Scroll to Top