Mols.gov.et

mols mols

News

የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ አህጉራዊ ጉባኤ በአዲስ አበባ …

የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ አህጉራዊ ጉባኤ በአዲስ አበባ ሊካሄድ ነው
በአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራን በተግባራዊ ፖሊሲዎች ለመደገፍ ያለመ አህጉራዊ ጉባኤ ለመጀመሪያ ጊዜ ሰኔ 4 እና 5 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይካሄዳል።
የተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ኢሲኤ) ያዘጋጀው ይህ ጉባኤ በአካዳሚክ ምርምሮች እና በፖሊሲ አፈጻጸሞች መካከል ያለውን ክፍተት መሙላትን ታሳቢ ያደረገ ነው።
የአፍሪካ ልማትና የተግባራዊ መፍትሄዎች መድረክ (ADIF 2026) የሚል ስያሜ ያለው ጉባኤ “በአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማሳደግ የሚረዱ ምርጥ ተሞክሮዎችና የፈጠራ መፍትሔዎች” በሚል መሪ ሀሳብ የሚካሄድ ነው።
ጉባኤው በአፍሪካ በፍጥነት እያደገ የሚገኘውን የወጣት ማኅበረሰብ፣ በዓመት ከ15 ሚሊዮን በላይ የሥራ ዕድል በመፍጠር አህጉራዊው ፍላጎትን ለመመለስ ከተያዘው ውጥን ጋር በቀጥታ የተገናኘ ነው።
ይህ አዲስ መድረክ ከተለመዱ አህጉራዊ ስብሰባዎች በተለየ፤ የፖሊሲ አፈጻጸምን በማፋጠን በዘርፉ ያለውን የፖሊሲ እና የአሰራር ሂደት ለማቀለጣፈ ያለመ መሆኑን ኢዜአ ከኢሲኤ ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
በዚህም መሠረት የኢኮኖሚክ ኮሚሽኑ በገንዘብ እጥረት ምክንያት መሬት ያልወረዱ ጥናታዊ ምርምሮችን ወደ ተግባር ለመለወጥ፣ በጥቂት አካባቢዎች ተሞክረው ስኬታማ የሆኑ አነስተኛ የሙከራ ፕሮጀክቶችን ለማስፋት እንዲሁም አህጉር በቀል ምርጥ ተሞክሮዎችን በአገራት አጠቃላይ የኢኮኖሚ ፖሊሲዎች ውስጥ በቀጥታ ለማካተት አቅዷል።
አሠራሩ በልማት ላይ የሚፈሱ የአህጉሪቱ ኢንቨስትመንቶች አስተማማኝና ዘላቂ ውጤት እንዲያመጡ ለማድረግ ትልቅ እገዛ ይኖረዋል ተብሏል።
የፎረሙን ውጤታማነትና ተጠያቂነት በተረጋገጠ መልኩ ለመከታተልም፣ ከጉባኤው በፊት፣ በጉባኤው ወቅትና ከጉባኤው በኋላ የሚተገበር የአሠራር ሥርዓት ተዘርግቷል።
የመድረኩን ቀጣይነትና ትስስር አስተማማኝ ለማድረግ፣ የየዓመቱ መሪ ሀሳቦችን አንዱ ከሌላው ጋር በማስተሳሰር እና ተመጋጋቢ በማድረግ እንደሚዘጋጁ ኮሚሽኑ አስታውቋል።
በቀጣይ የሚካሄዱት ፎረሞች፤ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና (AfCFTA) ትግበራን ከአህጉራዊ የኢንዱስትሪ ልማት ስትራቴጂዎች ጋር ማስተሳሰር ጨምሮ ሌሎች የልማት የትኩረት መስኮችን ታሳቢ በማድረግ እንደሚካሄዱ ተመላክቷል። መረጃው የኢዜአ ነው።

Read More »
News

እሴት ሰንሰለትን መሠረት ያደረገ የሥራ ዕድል ፈጠራ

እሴት ሰንሰለትን መሠረት ያደረገ የሥራ ዕድል ፈጠራ ውጤት አምጥቷል
በሶማሌ ክልል እሴት ሰንሰለትን (Value-Chain) መሠረት ያደረጉ የሥራ ፈጠራ ተግባራት ውጤት እያስመዘገቡ መሆኑ ተገለጸ።
የሱማሌ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ወ/ሮ ሂቦ አህመድ ፤ ሥራዎቹ በፌዴራል መንግስት የሥራ ፈጠራ ፖሊሲዎችና የሪፎርም ሃሳቦች መሠረት የተከናወኑ መሆኑን ገልጸው ተግባራቱ የክልሉ መንግስት ለወጣቶች ሥራ ፈጠራና ለአካባቢ ኢኮኖሚ ማነቃቂያ ያለውን ጽኑ ቁርጠኝነት ያሳዩ መሆኑንም ጠቁመዋል።
እንደ ወ/ሮ ሂቦ አህመድ ማብራሪያ፣ የገበያ ተኮር የልማት አቅጣጫን መሠረት ያደረገው ይህ ፕሮግራም በጅግጅጋና በጎዴ ከተሞች በሙከራ ደረጃ ተተግብሯል። ፕሮግራሙ በወተት፣ በእንቁላል፣ በሽንኩርትና በሥጋ ምርቶች አቅርቦት ላይ ትኩረት አድርጎ ተሰርቷል።
በሂደቱ 28 አቅራቢዎች (Supply Side) እና 22 ፈላጊዎች (Demand Side) በማስተሳሰር ከ2,200 በላይ ለሚሆኑ የአካባቢው ማህበረሰብ አባላት በትስስሩ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል፡፡
ይህ አሰራር የአካባቢውን የምርት አቅርቦት ሥርዓት እና የገበያ ትስስር በእጅጉ ከማሻሻሉም በላይ ለአምራቾች አስተማማኝ ገቢ መፍጠሩንና የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ማሳደጉን ገልጸዋል።
ሂደቱም ክልሉ ወደ ዘላቂና ገበያ-ተኮር የሥራ ፈጠራ ሥርዓት እየተሸጋገረ መሆኑን የሚያሳይ ነው ብለዋል።

Read More »
News

የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከፍተኛ አመራሮችና ሠራተኞች

የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከፍተኛ አመራሮችና ሠራተኞች «የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነፃነት» አገራዊ ኤግዚቢሽን ጎበኙ
ኤግዚቢሽኑ በኢትዮጵያ አስተማማኝ፣ ዘመናዊና የተቀናጀ የስታቲስቲክስ መረጃ ሥርዓት ለመገንባት የተከናወኑ አበይት ተግባራትን ይፋ ያደረገ ሲሆን፤ በመረጃና በማስረጃ ላይ የተመሠረቱ ፖሊሲዎችንና የልማት ዕቅዶችን ለመቅረጽ የተከናወኑ ስኬታማ ሥራዎች ለዕይታ በቅተውበታል።
በጉብኝቱ ወቅት እንደተገለጸው፤ መረጃ አገራዊ ራዕይ የሆነውን ጠንካራ ሀገረ መንግሥት የመገንባትና የፖሊሲ ሉዓላዊነትን የማረጋገጥ ጉዞ ዋነኛ ግብዓት ነው።
የዜጎችን እውቀትና ክህሎት በተደራጀ መንገድ በመጠቀም መረጃዎችን በሳይንሳዊ መንገድ የመሰብሰብ፣ የመተንተን እና በመረጃ ላይ የተመሠረቱ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን የማውጣት ልምድን ለማሳደግ የሚያስችል ሰፊ መሠረት እየተጣለ እንደሚገኝ ተመላክቷል።
ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱም ይህንን አገራዊ ራዕይ ለማሳካትና በክህሎት ልማት፣ በሥራ ዕድል ፈጠራና በኢንዱስትሪ ሰላም ዙሪያ የሚወጡ ፖሊሲዎችና ዕቅዶች ትክክለኛ መረጃን መሠረት ያደረጉ እንዲሆኑ በትኩረት እየሠራ መሆኑ ተገልጿል።

Read More »
News

ሥራ አጥነትን ለመቅረፍ ስታርትአፖችን …

ሥራ አጥነትን ለመቅረፍ ስታርትአፖችን በሳይንሳዊ መንገድ መደገፍ አማራጭ የሌለው ጉዳይ ነው።
ክቡር አቶ ሰለሞን ሶካ
የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከኤስ ኤንቪ ሊዌ ፕሮግራም ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የብሩህ ኢትዮጵያ 2025 የስታርትአፖች ቡትካምፕ የግምገማ እና የዕቅድ ማረጋገጫ መድረክ ተካሄደ።
በመድረኩ ላይ የሥራ ፈጣሪዎችን ተወዳዳሪነትና ክፍተቶች በዘላቂነት ለመፍታት የሚያስችል ሳይንሳዊ ጥናት ቀርቦ ሰፊ ውይይት ተደርጎበታል።
በመርሃ-ግብሩ ላይ የተገኙት የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር አቶ ሰለሞን ሶካ እንደገለጹት፤ ከማክሮ ኢኮኖሚ ዋና ዋና ፈተናዎች መካከል አንዱ የሆነውን ሥራ አጥነት በዘላቂነት ለመቅረፍ ስታርትአፖችን በሳይንሳዊ መንገድ መደገፍና ምቹ ሥነ-ምህዳር መፍጠር አማራጭ የሌለው ጉዳይ ነው።
ክቡር ሚኒስትር ዴኤታው አክለውም፣ በኢንተርፕረነርሺፕ ልማት ኢንስቲትዩት (EDI) በተጠናው ጥናት መሠረት ውጤታማነታቸው የተረጋገጠ እና ለአገር ውስጥ ገበያ ተግባራዊ መፍትሔ ይዘው የቀረቡ ስታርትአፖችን የፋይናንስ ተቋማት በባለቤትነት ሊደግፏቸው እንደሚገባ አሳስበዋል።
ተቋማቱ ለሥራ ፈጣሪዎች አስፈላጊውን የብድርና የፋይናንስ አቅርቦት በማመቻቸት ማህበራዊ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል።
የኢንተርፕረነርሺፕ ልማት ኢንስቲትዩት (EDI) ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ቦሩ ሸና በበኩላቸው፣ ጥናቱ ስታርትአፖች ከቡት ካምፕ ስልጠና በኋላ ቢዝነሳቸውን ወደ ተግባር ለመቀየር ያሉባቸውን ተጨባጭ ክፍተቶችና ፍላጎቶች ለመለየት ታስቦ የተሰራ መሆኑን አስገንዝበዋል።
በመድረኩ የተሳተፉ ባለድርሻ አካላት እንደጠቆሙት፤ በአሁኑ ወቅት ለስታርትአፖች ዕድገት ማነቆ የሆኑትን የፋይናንስ አቅርቦት፣ የሥራና ማምረቻ ቦታ፣ የገበያ ትስስር እና የብድር ዋስትና የመሳሰሉ ተግዳሮቶችን ለመቅረፍና ምቹ የፈጠራ ሥነ-ምህዳር ለመገንባት የሁሉንም አካላት የተቀናጀ ተሳትፎ ይጠይቃል።
ውድድሩን በፋይናንስ የደገፈው SNV በቀጣይም የፋይናንስ፣ የቢዝነስ ልማት (BDS) እና ሌሎች ዘርፈ-ብዙ ድጋፎችን ማድረጉን የሚቀጥል ሲሆን፤ ሚኒስቴሩም የስታርትአፕ አዋጅን እና የ”ዲጂታል ኢትዮጵያ” ስትራቴጂን ስኬታማ ለማድረግ ከፖሊሲ አውጪዎች፣ ከፋይናንስ ተቋማትና ከአለም አቀፍ አጋሮች ጋር ያለውን ስልታዊ ቅንጅት አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገልጿል።

Read More »
News

ኮሌጁ በዘርፉ የተደረገው ሪፎርም ተጨባጭ ውጤት እንዲያስመዘግብ …

ኮሌጁ በዘርፉ የተደረገው ሪፎርም ተጨባጭ ውጤት እንዲያስመዘግብ ያስቻለው መሆኑን አስታወቀ
በአዲስ አበባ የልደታ ማኑፋክቸሪንግ ኮሌጅ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር በዘርፉ የቀረፀውን የሪፎርም አጀንዳ ወደ መሬት በማውረድ ተጨባጭ ሽግግር ውጤቶች ማስመዝገቡን አስታውቋል።
ኮሌጁ ባወጣው መረጃ፤ ስልጠናን ከገበያ ፍላጎትና ከተግባራዊ የኢንተርፕራይዝ ድጋፍ ጋር በማጣመር የተከናወኑ ተግባራት የጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞችን አቅም በመገንባት፣ ወደ መካከለኛና ከፍተኛ አምራችነት እያሸጋገረ ይገኛል።
የኮሌጁ የኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽን እና ቴክኖሎጂ ልማት ምክትል ዲን አቶ ታከለ ኩሙላ እንደገለጹት፤ ተቋሙ የቴክኖሎጂ ሽግግር ስራዎችን በቀጥታ ከኢንዱስትሪዎች እና ከኢንተርፕራይዞች ተጨባጭ ፍላጎት በመነሳት እየሰራ ይገኛል።
በዚህም በተያዘው በጀት ዓመት ብቻ አስር አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ሰርቶ ማሸጋገር መቻሉን ተመላክቷል፡፡
ኮሌጁ ባደረገው የውጤት ዳሰሳ ጥናት፤ ባለፈው ዓመት የተሸጋገሩ ቴክኖሎጂዎች ለኢንተርፕራይዞች ከ749 ሺህ ብር በላይ አዲስ ሀብት ማፍራት አስችለዋል፡፡ ይህንን ውጤት እስከ በጀት ዓመቱ ማብቂያ ድረስ ወደ አንድ ሚሊዮን ብር ለማሳደግ ታቅዶ እየተሰራ እንደሚገኝም ነው የተገለፀው፡፡
ኮሌጁ የስልጠናና ድጋፍ ስራዎቹን ከግል ተቀጣሪነት ወደ ስራ ፈጣሪነት በሚያሸጋግሩ የተግባራዊ ኢንኩቤሽን ማዕቀፎች ላይ ያተኮረ ነው ተብሏል፡፡
አሁን ላይ ኮሌጁ ለይቶ ከሚደግፋቸው 859 ኢንተርፕራይዞች መካከል 243ቱ ቀጣይነት ያለው የካይዘን፣ የቢዝነስ ማኔጅመንት እና የማርኬቲንግ ድጋፍ በየሳምንቱ እንደሚያገኙም የኮሌጁ መረጃ ያመለክታል።
ኮሌጅ በወጣው መረጃ፤ የዘርፉ አዲስ እሳቤ ሀገራዊ ምርትን ከማሳደግ፣ የውጭ ምንዛሬን ከመተካት እና ለወጣቶች የሥራ ዕድል ከመፍጠር አኳያ ተጨባጭና አመርቂ ውጤት እያመጣ ይገኛል፡፡ በመሆኑም ስትራቴጂውን ይበልጥ አጠናክሮ ለማስቀጠል በትኩረት ርብርብ እየተደረገ ይገኛል፡፡

Read More »
News

የኢንተርፕረነርሺፕ ሥነ-ምህዳሩን ለማስፋት …

የኢንተርፕረነርሺፕ ሥነ-ምህዳሩን ለማስፋት የሚደረገውን ጥረት የሚያሳድገው የፐብሊክ ሰርቪስ ኢኖቬሽን ማዕከል ሥራ ጀመረ
የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ክብርት ሙፈሪሃት ካሚል፣ የኢትዮጵያ ኢንተርፕረነርሺፕ ልማት ኢንስቲትዩት ያስገነባውን የፐብሊክ ሰርቪስ ኢኖቬሽን ማዕከል መርቀው በይፋ ወደ ሥራ አስገብተዋል።
ማዕከሉ በሀገሪቱ የሥራ ፈጠራ ሥነ-ምህዳሩን ለማስፋትና የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን በፈጠራ ለማዘመን የሚደረገውን ጥረት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያግዝ ተገልጿል።
በምርቃት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ክብርት ሚኒስትር እንደገለፁት፤ ማዕከሉ ለፈጠራና አዳዲስ እሳቤዎች መፈለቂያ የሚሆን ነጻና ምቹ ከባቢን ይፈጥራል።
ኢንስቲትዩቱ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ላለፉት ዓመታት በኢንተርፕረነርሺፕ ሥነ-ምህዳር ግንባታ ላይ ደማቅ አሻራ እያሳረፈ መሆኑን አውስተው ወደ ሥራ የገባው ማዕከል ዜጎች ለሀገር የሚጠቅሙ አዳዲስ መፍትሄዎችን በተቀናጀና በተደራጀ አግባብ እንዲያፈልቁ ሰፊ ዕድል እንደሚከፍት ጠቁመዋል።
“ለሃሳብ ክብር ሲሰጥ ሀገር በፈጠራ አቅሞች ይጥለቀለቃል፣ ሀገርም ያድጋል” ያሉት ክብርት ሚኒስትር፣ መንግስት የብሔራዊ ኢንተርፕረነርሺፕ ልማት ፖሊሲን በማጽደቅ ሥነ-ምህዳሩን ለመገንባት የወሰነው የሃሳብን ክቡርነት በመገንዘብና ዘርፉን በህጋዊ ማዕቀፍ ለመምራት ካለው ጽኑ ቁርጠኝነት የተነሳ መሆኑን አስገንዝበዋል።
ሀገር የሚቀይር ሃሳብ ይዘው የሚለፉ ዜጎችን በተቋም ደረጃ መደገፍ መቻሉ፣ ባለሙያዎቹ የበለጠ እንዲበረቱና እንዲነቃቁ ትልቅ አቅም እንደሚሆንም አክለዋል።
ተቋሙ ተደራሽነቱን በማስፋት ከአፍሪካ ሀገራት ጋር ጭምር በትብብር ለመስራት በትኩረት እየተንቀሳቀሰ መሆኑንም አመላክተዋልዋል። ይህም ኢትዮጵያ በዚህ ዘርፍ የምታከናውናቸው ስራዎች ቀጣናዊ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ መሆናቸውን ያሳያል።
የሀገሪቱ የፈጠራ፣ የሥራ ዕድል ፈጠራ እና የክህሎት ልማት ጥረቶች ሁሉ እርስ በርስ ተሰናስለው የኢትዮጵያን የብልጽግና ራዕይ እውን ማድረግ እንዲችሉ፣ ሁሉም ዜጋና ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን ሚና እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል።

Read More »
News

አስቸኳይ የጥንቃቄ መልዕክት!

አስቸኳይ የጥንቃቄ መልዕክት!
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከፊውቸር ፊት ኢንተርናሽናል (Future Fit International) እና ከካናዳ ኤምባሲ ጋር በመተባበር ዜጎችን አሰልጥኖ ወደ ካናዳ ለመላክ የሚያስችል ስምምነት ሚያዝያ 1 ቀን 2018 ዓ.ም መፈራረሙ ይታወሳል።
👉 ሆኖም ይህንን ተከትሎ፣ አንዳንድ ሕገ-ወጥ አካላት የሚከተሉትን የፈጠራ ወሬዎች በማህበራዊ ሚዲያ እያሰራጩ ይገኛሉ፦
• ሰው ሰራሽ አስተውሎትን (AI/Deepfake) በመጠቀም የተፈበረኩና አሳሳች ምስሎችንና በቨዲዮዎችን ማሰራጨት 📽️
• “ምዝገባ ተጀምሯል” የሚሉ ሀሰተኛ መረጃዎችን በመልቀቅ ማህበረሰቡን ማደናገር፣
• በግል ስልክ ቁጥሮች ደውሉ በማለት ዜጎችን ለኢኮኖሚያዊ ብዝበዛ መጋበዝ 📞
እነዚህ ማስታወቂያዎች ሙሉ በሙሉ የማጭበርበር ተግባራት መሆናቸውን እናሳውቃለን። 🚫
❗ ትኩረት የሚሹ ነጥቦች፦
• በአሁኑ ወቅት ለካናዳ የሥራ ስምሪት ምንም አይነት ይፋዊ ምዝገባ አልተጀመረም፣
• በግል ስልክ ቁጥሮች የሚደረጉ ጥሪዎችም ሆኑ የሚላኩ አጫጭር መልዕክቶች (SMS) ሚኒስቴሩን አይወክሉም!
✅ የምዝገባ ጥሪ የሚደረገው
👉በብሔራዊ የቴሌቪዥንና የሬዲዮ ጣቢያዎች፤
👉የሚኒስቴሩን ይፋዊ የማረጋገጫ ምልክት (Blue Badge) ባላቸው ማህበራዊ ትስስር ገጾች ብቻ
🚫 ሊወሰዱ የሚገቡ ጥንቃቄዎች
• ለማያውቁት ወይም በግል ስልክ ቁጥር ለሚደረግ ጥሪ ምላሽ አይስጡ፤
• በማንኛውም ሁኔታ የገንዘብ ክፍያ አለመፈጽም፤
• ምንጫቸው ያልተረጋገጡ መረጃዎችን በማሰራጨት የጥፋቱ ተባባሪ አይሁኑ
✅ ምን ማድረግ ይገባዎታል?
✔️ መረጃዎችን ከሚኒስቴሩ ይፋዊ የመገናኛ ዘዴዎች ብቻ ያረጋግጡ፤
✔️ አጠራጣሪ እንቅስቃሴዎችን ሲመለከቱ ለሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ( 9138 በነፃ የስልክ መስመር ወይም info@mols.gov.et ) እና በአቅራቢያዎ ለሚገኙ የህግ አስከባሪ አካላት ይጠቁሙ።
📢 አስቸኳይ
📍 ዜጎች ከዲጂታል ማጭበርበርና ከሀሰተኛ መረጃዎች ራሳቸውን እንዲጠብቁ በጥብቅ እናሳስባለን!

Read More »
News

የሥራ ዕድል ፈጠራ ሥራውን ከዕቅድ በላይ ማሳካቱን ቢሮው አስታወቀ

የሥራ ዕድል ፈጠራ ሥራውን ከዕቅድ በላይ ማሳካቱን ቢሮው አስታወቀ
የአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ የ10 ወራት ዕቅድ አፈፃፀሙን ከባለድርሻና አስፈፃሚ አካላት ጋር ገምግሟል።
በዚህም ለ320,000 በላይ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን አስታውቋል። ይህም ከዕቅዱ አኳያ 111 በመቶ እንደሆነ ነው የተገለፀው።
በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ክቡር አቶ ሚሊዮን ማቴዎስ በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፣ ትልቁ ሪፎርም መዋቅር መቀየር ሳይሆን በአመራሩና በአስተግባሪው ዘንድ የሚፈጠር የአስተሳሰብ ለውጥ ነው ብለዋል።
በሥራ ዕድል ፈጠራ ወቅት የሥራ ማማረጥ ችግር እንደ ዋነኛ ተግዳሮት የታየ መሆኑን አመላክተው ቢሮው ለወላጆችና ለሥራ ፈላጊዎች የአመለካከት ቀረጻ ንቅናቄ መደረጉ ትርግም ያለው ውጤት ማምጣቱን አመላክተዋል።
ባለፉት 10 ወራት በቢሮው ለሥራ ዕድል ፈጠራ ሥራው የ2.2 ቢሊዮን ብር የብድር አቅርቦትና የሥራ ቦታዎች ማመቻቸት መቻሉን ከቢሮው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

Read More »
News

የሥራ ቦታዎች ምቹ መሆን ለምርታማነትና ለዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ

የሥራ ቦታዎች ምቹ መሆን ለምርታማነትና ለዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ

‎በኢትዮጵያ የቡና እና የሆርቲካልቸር የዕሴት ሰንሰለቶች ውስጥ ምቹ የሥራ ሁኔታን (Decent Work) ለማረጋገጥና ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ የተዘጋጀው ሀገራዊ የፕሮጀክት ዓብይ ኮሚቴ የመጀመሪያ ስብሰባውን በአዲስ አበባ አካሂዷል።
‎የሥራ ቦታዎች ምቹ እንዲሆኑ ማድረግ ምርትና ምርታማነትን ከማረጋገጥ ባለፈ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትንና ተገቢውን የገበያ ድርሻ ለማግኘት ያስችላል ሲሉ በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የአሰሪና ሠራተኛ ጉዳይ ዘርፍ ሚኒስትር ድኤታ ክቡር አቶ ዳንኤል ተሬሳ በጉባኤው መክፈቻ ላይ ገልፀዋል።
‎በኢትዮጵያ ቡና እና ሆርቲካልቸር የዕሴት ሰንሰለቶች ምቹ የሥራ ሁኔታን ማሻሻል ፕሮጀክት በአውሮፓ ህብረት የገንዘብ ድጋፍ በሥራና ክህሎት ሚኒስቴርና በዓለም አቀፍ የሥራ ድርጅት (ILO) አማካኝነት በኦሮሚያ፣ በደቡብ ኢትዮጵያና ከሲዳማ ክልሎች ይተገበራል፡፡
‎የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ምቹ የሥራ ሁኔታን (Decent Work) በሀገሪቱ ለማረጋገጥ የአምስት ዓመት ስትራቴጂ ቀርፆ እየተገበረ ይገኛል።
ይህም በአዲሱ የሪፎርም አስተሳሰብ የሥራ ቦታዎች ሰላምን በማረጋገጥ፣ የሠራተኞችን ደህንነትና ጤንነት በመጠበቅ ምርትና ምርታማነትን ለማረጋገጥ የተያዘውን ግብ የሚያጠናክር ነው።

‎በመድረኩ ላይ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴርን ጨምሮ የሚመለከታቸው ሚኒስቴር መ/ቤቶችና የዘርፉ ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል፡፡

በፕሮጀክቱ ትግበራ ላይ በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ፣ በአሰሪዎች፣ በሠራተኞች እና በአጋር ድርጅቶች መካከል የሚፈጠረው ቅንጅት ግልጽነትና ተጠያቂነት እንዲሰፍን፣ የሥራ ሁኔታ ምቹነት እንዲረጋገጥ፣ በሥርዓተ-ጾታ እኩልነት እና በሕፃናት ጉልበት ብዝበዛ ዙሪያ የሚታዩ ተግዳሮቶችን በዘላቂነት እንዲፈቱ እንደሚያግዝ ተገልጿል።

‎በመንግሥትና በማህበራዊ አጋሮች መካከል የሚፈጠር ጠንካራ ቅንጅት የግብርና ምርት ምሰሶ የሆነውን የቡና እና የአትክልት ምርቶቻችን ያለችግር ኤክስፖርት ለማድረግ የሚያስችል የ(Labor Compliance) ተፈፃሚነት በማሳደግ፣ የተሻለ የሥራ ዕድል ለመፍጠርና ዘላቂ የሆነ አገራዊ የኢኮኖሚ ዕድገት ለማምጣት ቁልፍ መሣሪያ መሆኑ ተመላክቷል።

Read More »
News

በድሬደዋ የወጣቶችን የስራ ዕድል ተጠቃሚነት…

በድሬደዋ የወጣቶችን የስራ ዕድል ተጠቃሚነት ያሳደጉ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ -ከንቲባ ከድር ጁሃር
በድሬደዋ ከተማ አስተዳደር የወጣቶችን የስራ ዕድል ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ከንቲባ ከድር ጁሃር ገለጹ።
የሀገር ውስጥና የውጭ አገራት የስራ ስምሪትን ለማመቻቸት ያለመ የአሰሪና ሰራተኞች አገናኝ ዐውደ ርዕይ ዛሬ በድሬደዋ ተካሂዷል።
የአስተዳደሩ ከንቲባ ከድር ጁሃር በወቅቱ እንዳሉት በድሬደዋ የወጣቶችን የስራ ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት በግብርና፣ በኢንዱስትሪ፣ በአገልግሎትና በሌሎችም ዘርፎች አማራጮችን በማስፋት ላይ ይገኛል።
ተግባሩን ለማስቀጠልም ከአጋር አካላት ጋር በመቀናጀት በተለያዩ የሙያ መስኮች የሰለጠኑ 350 ወጣቶች በመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት የስራ እድል እንዲያገኙ መደረጋቸውን ገልጸው፤ ለዚህም የዛሬው መርሃ ግብር መዘጋጀቱን ጠቁመዋል።
በተጨማሪም በሀገር ውስጥ የስራ ስምሪት ለሚሳተፉ ወጣቶችም በአሰሪና ሰራተኞች አገናኝ ድርጅቶች አማካኝነት 380 ለሚሆኑ ወጣቶች የስራ እድል መመቻቸቱን ገልጸዋል።
የድሬደዋ አስተዳደር የስራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሮቤል ጌታቸው በበኩላቸው ወጣቶች በዕውቀትና በክህሎት ተወዳዳሪ በመሆን የስራ እድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
ለዚህም ሴክተር መስሪያቤቶች እና ባለሃብቱ በቅንጅት እንዲሰሩ የተለያዩ መድረኮች መካሄዳቸውን ጠቁመው የአሁኑ ዐውደ ርዕይም የቅንጅታዊ ስራው ማሳያ ነው ብለዋል።
ከሀገር ውስጥ የስራ ስምሪት ባለፈ ወደ ውጭ ሀገራት ለሚጓዙት ወጣቶች የቋንቋ፣ የአካባቢዎቹ መረጃዎችና ሙያዊ ስነምግባር ላይ ተገቢውን ስልጠና በመውሰድ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ መሰራቱን አንስተዋል። ዘገባው ኢዜአ ነው።

Read More »
The Minister Is answering questions live in zoomClick To join the live Meeting
+
en_USEN
Scroll to Top