Mols.gov.et

mols mols

News

የልል ክህሎት(soft skills) ግንባታ- ለሥልጠና ጥራት

የልል ክህሎት(soft skills) ግንባታ- ለሥልጠና ጥራት
የኢፌዴሪ ቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት በየሳምንቱ የሚያካሂደው የጥናትና ምርመር መርሃ ግብር በቴክኒክና ሙያ ስልጠና ሥርዓት ውስጥ የልል ክህሎት(soft skills) ግንባታ አስፈላጊነት ላይ ያተኮሩ የዳሰሳ ጥናቶች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡
በጥናቱ በቴክኒክና ሙያ ተቋማት ውስጥ የእንግሊዘኛ ቋንቋ ስልጠና ስርዓት በሚጠበቀው ደረጃ ያለመሆኑ በዋነኛነት በስልጠና ሥርዓቱ ላይ ተፅዕኖ እንዳሳደረ ተገልጿል፡፡
በቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ዘርፍ ላለፉት 20 አመታት የእንግሊዘኛ ትምህርት ከስልጠና ፕሮግራምነት ውጪ ሆኖ መቆየቱ የሰልጣኞች የእንግሊዘኛ ቋንቋ ችሎታ ዝቅተኛ እንዲሆን እንዳደረገውና ይህም ለዘርፉም ዋነኛ ተግዳሮት ሆኖ መቆየቱ ተጠቁሟል፡፡
ሰልጣኞች የቋንቋ ክህሎት ላይ የሚታየው ክፍተት በእንግሊዘኛ የሚዘጋጁ የትምህርት መርሃግብሮችን፣ መመሪያዎች እና ቴክኒካል የሆኑ ቃላቶችን ለመረዳት አስቸጋሪ እንደሚሆንባቸው ጥናቱ ያመላከተ ሲሆን ይህም በስልጠና ጥራት ላይ ጉልህ ተፅዕኖ እንደሚያሳርፍ ተብራርቷል፡፡
በመሆኑም ከሥልጠና ዘርፎች ጋር ሊጣጣም የሚችል የእንግሊዘኛ ቋንቋ ስርዓተ ትምህርት ተዘጋጅቶ አጠቃላይ የስልጠና ሂዱቱን መደገፍ የሚያስችል አሠራር መዘርጋት እንደሚኖርበትም ምክረ ሃሳብ ቀርቧል፡፡

Read More »
News

ከስልጠና በላይ…

ከስልጠና በላይ…
ስልጠና አጠናቃቂዎቹን ከሥራ ጋር በማስተሣሰር አብነት እየሆነ ያለው ኮሌጅ
በኮሪያ መንግስት ዓለም አቀፍ ትብብር ኤጀንሲ(ኮይካ) እና በኤልጂ ኤሌክትሮኒክስ ድጋፍ የተቋቋመ የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ተቋም ነው፣ ኤል ጂ ኮይካ ሆፕ የቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ፡፡
የሥራ ገበያውን ፍላጎትንእና የኤልጂን ኩባንያ ቁልፍ የሙያ ክህሎትችን፣ ብቃቶችንና ቴክኖሎጂዎችን መሰረት በማድረግ በኤሌክትሮኒክስ፣ በአይሲቲና ተዛማች መስኮች ጥራት ያለው ስልጠና በመስጠት ይታወቃል።
የኮሌጁ ዲን አቶ ታሪኩ ገብረ መድህን እንደሚገልፁት ስልጠናው በኤል ጂ የኤሌክትሮኒክስ አምራች ተቋም የጥራት ስታንዳርድ መሰረት የሚሰጥ ነው። ይህም ሰልጣኞችን በሥራ ገበያው ላይ የላቀ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ያደርጋቸዋል።
ኮሌጁ ከሥልጠና ባለፈ ለስልጠና አጠናቃቂዎቹ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የሥራ ዕድል በማመቻቸት ከሥራ ጋር እንዲተሣሰሩ ያደርጋል።
በዚሁ መሰረት በዱባይ ፣ በኬኒያ፣ በጅቡቲ እና በሞሪሺየስ በሚገኙ የኤል ጂ ኤሌክትሮኒክስ ቅርንጫፎች ውስጥ ብቁና ተወዳዳሪ ለሆኑ ባኮሌጁ ምሩቃን የሥራ ዕድል ማመቻቸት መቻሉንም አቶ ታሪኩ ይገልፃሉ።
ኮሌጁ ለስልጠና አጠናቃቂዎቹ የራሳቸውን ቢዝነስ አቋቁመው ወደ ሥራ እንዲገቡም አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል፡፡
ድጋፉ በኤሌክትሮኒክስ ጥገና ላይ መሠማራት ለሚፈልጉ ለሥራ መጀመሪያ የሚያስፈልጉ መሳሪያዎችን ማሟላትን ያካትታል፡፡ በዚሁ መሰረት በአዲስ አባባ ብቻ 123 ቢዝነሶች በኮሌጁ ምሩቃን ተከፍተው እየሠሩ እንደሚገኙ የኮሌጁ ዲን ጨምረው አሳውቀዋል፡፡
ተቋማት የኮሌጁን ሰልጣኖች ቢቀጥሩ የሚያገኙትን ጠቀሜታ የሚያመለክት መረጃ የያዘ መጽሐፍ(employment book) በኮሌጁ በየዓመቱ ተዘጋጅቶ ለተለያዩ ቀጣሪ ተቋማትና ኢንዱስትሪዎች ይሰራጫል፡፡
ይህም ቀጣሪ ተቋማት የሚፈልጉትን የሰው ኃይል በቀላሉ ለማግኘት እንደሚረዳቸው የሚናገሩት አቶ ታሪኩ በዚህ መልኩ ለኮሌጁ ምሩቃን የሥራ ዕድል አማራጮችን የማስፋት ሥራ እየሠራን እንገኛለን ብለዋል፡፡
በኮሌጁ ቅጥር ግቢ ውስጥ በየዓመቱ የሚዘጋጀው ሥራ አውደ ርዕይ(job fair) የኮሌጁ ምሩቃን አቅም ለቀጣሪ ተቋማት በማስተዋወቅ የሥራ ዕድል የሚመቻችበት ሌላው አማራጭ እንደሆነም አቶ ታሪኩ ይናገራሉ፡፡
የሥራ ገበያ መዳረሻዎችንም በማስፋት በኮሪያና በሌሎች ሀገራት ላይ ሰልጣኞችን በብቃትና በጥራት አሰልጥኖ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝም አመላክተዋል፡፡
የማህበራዊ ሃለፊነትን ከመወጣት አንጻርም ህብረተሰቡን የሚጠቅሙ የተለያዩ ሥራዎችን እንደሚሠራና በተለያዩ ግብረሰናይ ድርጅቶች ውስጥ ለሚገኙ የኤሌክትሮኒክስ ቁሳቁሶችና ማሽኖች ነፃ የጥገና አገልግሎት እንደሚሰጥ የኮሌጁ ዲን አመላክተዋል።
ሰልጣኞች የቀሰሙትን ክህሎት ወደ ተግባር በመቀየር ማህበረሰቡን የሚጠቅሙ ችግር ፈቺ ሥራዎችን እየሰሩ እንደሆነ በኮሌጁ የጥናትና ምርምር፣ የማህረሰብ አገልግሎት እና ኢንኩቤሽን ክፍል ሃላፊ አቶ ወንድምአገኝ አለምአየሁ ይናገራሉ።
ኮሌጁ የቴክኖሎጂ ሥራ ፈጠራን እንዲሁም የቴክኖሎጂ ንግድ ሐሳቦችን ማፍለቅና አዲስ የተቋቋሙ ሥራዎችን (Start-up) የመደገፍ አገልግሎት የሚሰጥ ዘመናዊ የኢንኩቤሽን ማዕከልንም አቋቁሟል ብለዋል።
በኮምፒውተርና የሞባይል ስልክ ጥገና፣ በግራፊክስና ኤዲቲንግ፣ በፕሮግራሚንግ፣ በፍሪጅ፣ በፎቶ ኮፒ ማሽን፣ በኤይር ኮንዲሽነር ማሽንና በቴሌቪዥን ጥገና ዘርፎች ላይ አጫጭር ስልጠናዎችን እየሰጠ እንደሚገኝ አቶ ወንድምአገኝ ተናግረዋል፡፡
በተለያየ ምክንያት እርዳታና ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ወጣቶች በኤሌክትሮኒክስ ኮሙኒኬሽን፣በመልቲሚዲያ፣ የአይሲቲ ሀርድዌር እና ኔትወርኪንግ ፕሮግራሞችን ነፃ ስልጠና በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡

Read More »
News

ዜጎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ ቅንጅታዊ አሰራርን ማጠናከር እንደሚገባ ተጠቆመ

ዜጎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ ቅንጅታዊ አሰራርን ማጠናከር እንደሚገባ ተጠቆመ
በሥራ ዕድል ፈጠራ ከፍተኛ ሚና ያላቸው የመንግስት የልማት ድርጅቶች እና የመንግስት ተቋማት የተሳተፉበት ብሔራዊ የቴክኒክ ኮሚቴ ውይይት ተካሄዷል፡፡
የመንግስት የልማት ድርጅቶች እና የመንግስት ተቋማት ቅንጅታዊ አሰራር በማጠናከር የሥራ ዕድል ፈጠራ ማነቆዎችን በጋራ መፍታትና በየተቋማቱ የሚገኙ የሥራ ዕድል ጸጋዎች አሟጦ በመጠቀም ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚገባም ተገልጿል፡፡
በመድረኩ የልማት ድርጅቶች እና ክልሎች የሥራ ዕድል ፈጠራ እቅድ አፈጻጸም ቀርቦ ውይይት የተካሄደ ሲሆን በኢንተርፕራይዝ ምስረታ እና በቅጥር የተፈጠሩ የሥራ ዕድሎች እንዲሁም ጠንካራ ቅንጅታዊ አሰራር በመዘርጋት ውጤታማ አፈጻጸም ያስመዘገቡ ተቋማት ተሞክሮአቸውን አጋርተዋል፡፡
ዜጎች በሥራ ዕድል ተጠቃሚ የማድረግ ጉዳይ ለአንድ አካል የሚተው ሳይሆን የሁሉም ባለድርሻ አካላት የጋራ ርብርብ የሚጠይቅ መሆኑ በመድረኩ አጽንኦት ተሰጥቶታል፡፡
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ሀገራዊ የሥራ ዕድል ፈጠራውን ሂደት የማስተባበር፣ የመከታተልና የመቆጣጠር ተልዕኮ የተሰጠው ተቋም መሆኑን ይታወቃል፡፡

Read More »
News

በክልሉ ባለፉት አራት ወራት ከ474ሺህ በላይ የሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸው ተገለፀ

በክልሉ ባለፉት አራት ወራት ከ474ሺህ በላይ የሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸው ተገለፀ
በኦሮሚያ ክልል በበጀት አመቱ አራት ወራት ከ474ሺህ በላይ ዜጎች በሀገር ውስጥና በውጪ ሀገራት የስራ ዕድል እንደተፈጠረላቸው የክልሉ የስራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ቢሮ አስታወቀ።
የቢሮው ምክትል ሀላፊ ዋስሁን ጎልጋ ለኢዜአ እንደተናገሩት በበጀት አመቱ በክልሉ የሚገኙ ስራ አጥ ዜጎችን የስራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ ነው።
በዚህም ከስራ አጥ ወጣቶች፣ ከወላጆች፣ ከኃይማኖት አባቶች፣ ከሀገር ሽማግሌዎች፣ ከአባ ገዳዎችና ከሃደ ሲንቄዎች ጋር የስራ ልየታና አመለካከት ላይ በማተኮር የግንዛቤ ማስረጽ ስራ መሰራቱን ተናግረዋል።
እንዲሁም መንግስታዊና መንግስታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች ጋርም ሰፊ መውይይት መደረጉንም ገልጸዋል።
በአጠቃላይ በበጀት አመቱ ለ2 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዜጎች የስራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን አስታውሰው፤ ባለፉት አራት ወራት ከ474ሺህ በላይ ዜጎች በሀገር ውስጥና በተለያዩ የውጪ ሀገራት የስራ ዕድል መፍጠር መቻሉን አስታውቀዋል።
የስራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች መካከል 416ሺህ 995 የሚሆኑት በሀገር ውስጥ የስራ ዕድል ተጣቃሚ መሆናቸውን አንስተው፤ 58ሺህ 741 ዜጎች ደግሞ በቂ ስልጠና ተሰጥቷቸው የብቃት ማረጋገጫ በማግኘት ወደተለያዩ ሀገራት መሰማራታቸውን ገልጸዋል።
በተለይም በገጠሩ አካባቢ ወደ ስራ ለገቡ ዜጎች በስፋት በግብርና ልማት ኢንሼቲቮች መሳተፋቸውን አንስተው በከተማም ያሉትን አማራጮች ለመጠቀም ተሞክሯል ብለዋል።
የስራ ዕድሉ የተፈጠረው በኢንቨስትመንት፣ በጨርቃጨርቅ፣ በአገልግሎት፣ በግብርና ምርት ማቀነባበር፣ በጎጆ እንዱስትሪዎች፣ በብረታብረት፣ በእንጨትና እንጨት ውጤቶች ዘርፍ መሆኑን አብራርተዋል።
እንዲሁም በእንስሳት እርባታ፣ በወተት ልማት፣ በዶሮ እርባታ፣ በፍራፍሬና አትክልት ልማት መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል።
የስራ ዕድል የተፈጠረላቸው ዜጎች በሚሰማሩበት የስራ መስክ ውጤታማ እንዲሆኑ ክህሎት መር ስልጠና መሰጠቱን ጠቁመው ለሥራ ማስኬጃ የሚሆን ስምንት ቢሊዮን ብር ብድር መቅረቡን ተናግረዋል።
በተጨማሪም 15ሺህ ሄክታር መሬትና 2ሺህ 500 የማምረቻና መሸጫ ቦታዎች መሰጠቱን አስታውቀዋል።
በቀጣይም የተያዘውን ዕቅድ ለማሳካት ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት የተጀመሩ ስራዎች ይጠናከራሉ ብለዋል። ዘገባው የኢዜአ ነው፡፡

Read More »
News

ለአዳዲስ ተመዝጋቢ ሰልጣኞች የሳይኮሜትርክስ ምዘና …

ለአዳዲስ ተመዝጋቢ ሰልጣኞች የሳይኮሜትርክስ ምዘና …
የሳይኮሜትርክስ ምዘናው በባህር ዳር፣ በደብረታቦር እና በቦንጋ ፖሊ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ጨምሮ በተመረጡ የቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ኮሌጆች ተግባራዊ መደረጉን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
ምዘናው ለአዳዲስ ሰልጣኞች የሚሰጥ ሲሆን ሰልጣኞች የሙያ መስክ ሲመርጡ በፍላጎቶት ብቻ ሳይሆን ተሰጥኦና ዝንባሌያቸውን መሰረት በማድረግ ውጤታማ ሊሆኑባቸው የሚችሉ የሙያ መስኮች እንዲመርጡ የሚያግዛቸው ነው።
የሥልጠና ጥራትና አግባብነት እንዲሁም ውጤታማነትን ከሥራ ገበያ ፍላጎቱ ጋር በማጣጣም ብቁ፣ በቂና ተወዳዳሪ ሰልጣኞችን በማፍራት እንደ ሀገር ለሥራ ገበያው ፍላጎት ምላሽ የሚሰጥ የቴክኒክና ሙያ ስርዓት ባለቤት እንድንሆን የሚደረገው ጥረት አንዱ አካል ነው።

Read More »
News

የኢትዮጵያ ሥራ ፈጣሪ ወጣቶች ማኅበር እና የሳውዲ ዓረቢያው ተቋም ስትራቴጂያዊ ትብብር ፈጠሩ

የኢትዮጵያ ሥራ ፈጣሪ ወጣቶች ማኅበር እና የሳውዲ ዓረቢያው ተቋም ስትራቴጂያዊ ትብብር ፈጠሩ
የኢትዮጵያ ሥራ ፈጣሪ ወጣቶች ማኅበር (EYEA) እና የሳውዲ ዓረቢያ የአነስተኛ እና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ተቋማት ባለስልጣን (ሙንሻአት) በዲጂታል እና በኤሌክትሮኒክስ አገልግሎቶች ዘርፍ ትብብርን ለማሳደግ የሚያስችል ስትራቴጂያዊ ትብብር መፍጠራቸው ተገለጸ።
በሁለቱ ተቋማት መካከል የተደረገውን የመግባቢያ ስምምነትም የኢትዮጵያ ሥራ ፈጣሪ ወጣቶች ማኅበር ፕሬዝዳንት ሳሚያ አብዱልቃድር እና የ”ሙንሻአት” የጋራ ጉዳዮች ኃላፊ አቶ አብዱል ሙህሲን አል ሳሊም ተፈራርመዋል።
ስምምነቱን በሳውዲ ዓረቢያ የኢፌዴሪ ልዩ መልዕክተኛ እና ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ሙክታር ከድር (ዶ/ር) እና የ”ሙንሻአት” ዋና ገዥ የሆኑት አቶ ሳሚ ኢብራሂም አልሁሰይኒ በተገኙበት ተከናውኗል።
ይህ አጋርነት በአፍሪካ በተለይም በኢትዮጵያ እና በሳውዲ ዓረቢያ መካከል በሚገኙ ሥራ ፈጣሪዎች እና ስታርት አፖች መካከል ትርጉም ያለው ትብብርን ለማሳደግ ያለመ ነው።
ትብብሩ የእውቀትና የቴክኖሎጂ ሽግግርን፣ የጋራ ሥራዎችን፣ የአቅም ግንባታን እና ድንበር ተሻጋሪ የገበያ ተደራሽነትን ለማገዝ እንደሚረዳ ተመላክቷል።
በተጨማሪም የወጣቶችን ፈጠራ ለማሳደግ፣ ከወለድ ነፃ የፋይናንስ አሠራሮችን ለማስተዋወቅ እና ወጣቶች ሁሉን አቀፍ ዕድገትን እንዲያመጡ እንዲሁም የረጅም ጊዜ የልማት ግቦች ላይ አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ የሚያስችሉ ዘላቂ የሥራ ፈጠራ ሥርዓቶችን ለማጠናከር የሚያስችል ትብብር መሆኑ ተገልጿል።
በመጨረሻም በዚህ ስምምነት “ሙንሻአት” ከሁለቱም ወገን ያሉ ሥራ ፈጣሪዎች ውጤት በማስመዝገብ ዓለም አቀፍ ተሞክሮዎች እንዲጠቀሙ፣ በዓለም ዙሪያ ካሉ የሥራ ፈጣሪ ድርጅቶች ጋር ትብብርን እንዲያስፋፉ እና ለአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች እድገትና ዘላቂነት የሚያበረታታ የተቀናጀ የንግድ ከባቢን እንዲፈጥሩ እንዲሁም ከሳውዲ አረቢያ ራዕይ 2030 ዓላማዎች ጋር እንዲጣጣሙ የሚያስችል – ቀጠናዊ እና ዓለም አቀፍ ገበያዎችን እንዲያገኙ ለማስቻል የሚሰራ መሆኑ ተጠቅሷል።
የኢትዮጵያ ሥራ ፈጣሪ ወጣቶች ማኅበር የወጣቶችን የመፍጠር አቅም ለማጎልበት የሚሠራ ማኅበር ሲሆን፣ የማኅበሩ ዓላማ ለወጣት ሥራ ፈጣሪዎች የሚያስፈልጉ ግብዓቶችን እና ሃብት ማቅረብ እንዲሁም ቢዝነሶቻቸው ስኬታማ ይሆኑ ዘንድ የፈጠራ ሐሳቦችን የሚያገኙበትን ትስስሮችን መፍጠር ነው።
በስትራቴጂያዊ ምሰሶዎቹ እና ኢኒሼቲቮቹ አማካኝነትም ትብብርን፣ ፈጠራን እና ዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያበረታታ ሕያው ሥነ-ምኅዳር ለመገንባትም ይሠራል። ዘገባው የኢቢሲ ነው።

Read More »
News

ክፍለ ከተማው በአንድ ጀምበር 1 ሺህ 100 የሥራ ዕድል መፍጠሩን የአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ አስታወቀ

ክፍለ ከተማው በአንድ ጀምበር 1 ሺህ 100 የሥራ ዕድል መፍጠሩን የአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ አስታወቀ
የኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ አስተዳደር “በአንድ ጀምበር 1000 የስራ ዕድል” በሚል መሪ ሀሳብ የአንድ ጀንበር የሥራ ዕድል ፈጣራ ንቅናቄ አካሂዷል፡፡
ንቅናቄው በክፍለ ከተማው ባሉት ሁሉም ወረዳወቀች የሚመለከታቸውን ባለድርሻ አካላትን ባሳተፈ መልኩ ተካሂዷል፡፡ በዚህም ለ1100 ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር ተችሏል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ ሥራና ክህሎ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ ሚደቅሳ ከበደ በንቅ በንቅናቄው መርሀ ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ክፍለ ከተማው ባለድርሻ አካላትን አስተባብሮ ለወጣቶች ሥራ ዕድል መፍጠሩ ሊመሰገን ይገባል ብለዋል።
ወጣቶች መንግስት ባመቻቸላቸው የሥራ ዕድል ገቢያቸውን በማሻሻል የራሳቸውና የሀገራቸው ሊለውጡ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
የክፍለ ከተማው ዋና ስራ አስፈፃሚ ሀላፊ ተወካይ የሆኑት አቶ ሰይድ መሀመድ በበኩላቸው፤ ወጣቶች እውቀታቸውን እና ክህሎታቸውን ተጠቅመው ወደ ሥራ የሚገቡበት ሁኔታ እያመቻቸ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
በንቅናቄው ከተፈጠረው 1100 የሥራ ዕድል 61 በመቶ ወጣቶች መሆናቸውን ገልፀው ማኑፋክቸሪንግ፣ አገልግሎት፣ ንግድ እና ኮንስትራክሽን የሥራ ዕድሉ የተፈጠረባቸው ዘርፎች መሆናቸውን ከአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

Read More »
News

በማይታመን ፍጥነት በሁሉም ዘርፎች ውስጥ እየሰረፀ የሚገኘው አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ

በማይታመን ፍጥነት በሁሉም ዘርፎች ውስጥ እየሰረፀ የሚገኘው አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ
የኢፌዲሪ ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኢንስቲትዩት የጀመረውን አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ስልጠና ለማስተዳደር በሚያስችሉ ህጎችና ደንቦች ዙሪያ ያተኮረ ጥናት ኢኒስቲትዩቱ በየሳምንቱ በሚካሄደው ጥናትና ምርምር ጉባኤ ላይ ቀርቧል፡፡
የኢንስቲትዩቱ የጥናትና ምርምር እና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ሀብታሙ ሙሉጌታ ዓለም በአሁኑ ጊዜ እያስተናገደች የምትገኘውን የዕውቀት፣ የክህሎት፣ የቴክኖሎጂ ዕድገት ላይ ያተኮሩ ውይይቶች በየሳምንቱ እየተካሄዱ እንደሚገኙ ጠቁመዋል፡፡
ኢኒስቲትውቱ አዳዲስ እና ጠቃሚ የጥናትና ምርምር ርዕሰ ጉዳዮችን በመዳሰስ በተቋሙ የጀመረውን ፈጣን የሆነ የሪፎርም ሥርዓት በውጤታማነት እንደሚያስቀጥልም ተናግረዋል፡፡
አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ በሁሉም ዘርፎች ውስጥ እያደገ የመጣ ቴክኖሎጂ ሲሆን በተለይም እንደ ኢንስቲትዩቱ ያሉ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ውስጥ ያሉ ተመራማሪዎች ዘርፉን ስርዓት ባለውና በኃላፊነትን በተላበሰ ስሜት ለመጠቀም በሚያስፈልጉ ህጎች፣ ደንቦችና ሥርዓቶች ላይ አተኩሮ ጉባኤው ተካሂዷል፡፡
አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ሥራን በጥራትና በፍጥነት ለማከናወን ካለው ጠቀሜታ ባሻገር የሰው ልጅ ተጠቃሚነት ሳይጓደል ጎን ለጎን የቴክኖሎጂው ተጠቃሚ ለመሆን በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ከቀረበው የመነሻ ጥናት ላይ በመነሳት ሰፊ ውይይት ተካሂዷል፡፡
ከቴክኖሎጂው አጠቃቀም ረገድ ሌሎች ሀገራት ያጋጠማቸው አይነት ችግር ሀገራችንን እንዳይገጥማት ተሞክሮዎቻቸውን በመቅሰም ከወዲሁ ውጤታማ የአሠራር ሥርዓት መዘርጋት እንደሚያስፈልግም በስፋት ተነስቷል፡፡
በዕለቱ በ‹‹በኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ ውስጥ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስን በመጠቀም እንዴት የአየር ንብረት ብክለትን መቀነስ ቻላል ›› በሚል ርዕስ የተዘጋጀ ጥናታዊ ጽሁፍ ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል፡፡

Read More »
News

የሙያ ብቃት ምዘናና ሰርተፊኬሽን ስርዓቱ: አዲስ ምዕራፍ

የሙያ ብቃት ምዘናና ሰርተፊኬሽን ስርዓቱ: አዲስ ምዕራፍ
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የሙያ ብቃት ምዘናና ሰርተፊኬሽን ስርዓቱ የስልጠና አግባብነትንና ጥራትን በሚጠበቀው ልክ የሚያሻሽልና ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው ለማድረግ መሰረተ ሰፊ ሪፎርም እያካሄደ ይገኛል።
የሪፎርሙ ዋነኛ ትኩረት ተዓማኒ፣ ግልፅ፣ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ፣ በቴክኖሎጂ የሚታገዝ እና የኢንዱስትሪውን ባለቤትነት ያረጋገጠ ሀገራዊ የብቃት ምዘናና የምስክር ወረቀት አሰጣጥ ስርዓት በመዘርጋት ብቁ፣ ተወዳዳሪና አምራች ዜጎችን ለማፍራት የሚደረገውን ጥረት ማላቅ ነው።
በዚህም የሙያ ብቃት ምዘናና ሰርተፊኬሽን ስርዓቱን አውቶሜት ለማድረግ የሚያስችል የቅድመ ዝግጅት ስራው ተጠናቆ የትግበራ ሥራን ለማስጀመር በኦሮሚያ እና በሀረሪ ክልሎች የመጀመሪያ የአውቶሜሽን ሲስተም ስልጠና ተሰጥቷል። በቀጣይ በሁሉም ክልሎች የአውቶሜሽን ስርዓቱን ለመተግበር ከኢትዩጵያ ሥራ ገበያ መረጃ ስርዓት ኘሮጀክት ጽ/ቤት ጋር በጋራ የማብቃት ሥራ የምናከናውን ይሆናል።
እንዲሁም ሁሉንም የክልልና የሁለቱም ከተማ አስተዳድሮች የሙያ ብቃት ምዘና ኤጀንሲዎች ዓለም አቀፉን ISO 17024 እውቅና እንዲያገኙ ከኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩት ጋር የቃል ኪዳን ውል የተፈራረሙ ሲሆን፣ ሲዳማ፣ ኦሮሚያ እና አማራ ክልሎች ወደ ተግባር ሥራ የገቡ ክልሎች ናቸው።
በተጨማሪም የአዳዲስ የምዘና መሳሪያዎችን ዝግጅት እና የብቃት ምዘና መሳሪያዎች ብዝኃነትን ለማረጋገጥ ከክልሎች ጋር በመተባበር ቢያንስ አንድ ሙያ ከ4 በላይ ተጨማሪ ቨርዥን እንዲኖረው የማድረግ ሥራም እየተከናወነ እንደሆነ የሙያ ደረጃና ሥርዓተ ሥልጠና ዝግጅትና ብቃት ምዘና መሪ ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ ማርታ ወልዴ ገልጸዋል።

Read More »
News

እንተርፕራይዞች ሥራቸውን ለማሳደግ የሚገጥማቸውን ችግር ለመቅረፍ በትኩረት እየሠራ እንደሚገኝ ተጠቆመ

እንተርፕራይዞች ሥራቸውን ለማሳደግ የሚገጥማቸውን ችግር ለመቅረፍ በትኩረት እየሠራ እንደሚገኝ ተጠቆመ
በተለያየ ደረጃ የሚገኙ እንተርፕራይዞች ሥራቸውን ለማሳደግ የሚገጥማቸውን ችግር ለመቅረፍ ያለመ የውይይት መድረክ ተካሂዷል፡፡
በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የቴክኒክና ሙያ ዘርፍ የሥልጠናና የተቋማት አቅም ግንባታ መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሙህዲን አባ ሞጋ በመድረኩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፣ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና አጠናቃቂዎችና ኢንተርፕራይዞች ከሚገጥሟቸው ተግዳሮቶች መካከል አንዱ የሥራ መጀመሪያና ማስፋፊያ ካፒታል እጥረት ነው፡፡ ይህንን ችግር ለመቅረፍም መንግስት የተለያዩ ጥረቶችን በማድረግ ላይ ይገኛል ብለዋል፡፡
በዚህም የጥቃቅን አነስተኛ እና መካከለኛ እንተርፕራይዞች ቢዝነሳቸውን ለማሳደግ የሚያግዛቸውን የአቅም ግንባታ ሰልጠና የብድር አቅርቦት ላይ የሚገጥማቸውን ችግር ለመፍታት የሚያስችሉ ሥራዎች እየተሰሩ እንደሆነም አመላክተዋል፡፡
የብድር አቅርቦት ጋር ያሉ ችግሮችን ለመቅረፍ ከስድስት ባንኮች ጋር ያለማስያዣ ወጣት ሥራ ፈጠሪዎች ብድር የሚያገኙበት መንገድ ተመቻችቶ ወደ ሥራ መገባቱ እና በቅርቡም የወጣጦች የሥራ ፈጠራ ኢንቨስትመንት ባንክ ተቋቁሞ ወደ ሥራ መግባቱንም አስረድተዋል፡፡
ብድር የማግኘት ሂደቱ ከባንኮች መደበኛ የአሠራር ሂደት የተለየና ቀላል መሆን እንዳለበት፤ የንግድ ክህሎት ስልጠና የገንዘብ አያያዝና ብድር እንዲሁም የአቅም ግንባታ ሰልጠና መሰጠት እንዳለበት የመድረኩ ተሳታፊዎች አንስተዋል፡፡
ከማስተርካርድ ፋውንዴሽን ጋር በመተባበር በአነስተኛ ንግድ ሥራ ላይ ለተሰማሩ ወጣቶች ከባንኮች በቀላሉ ብድር አግኝተው ሥራቸውን በማስፋፋት የኢንተርፕራይዞችን የመሞት ምጣኔ ለማሰቀረት እየተሰራ መሆኑም በዕለቱ ተገልጿል፡፡
በመድረኩ ላይ ከአስራ አንዱ የአዲስ አበባ ከተማ ክፍለ ከተማዎችና እና ከ12ቱ ሸገር ከተማ አስተዳዳር የሥራ ማዕከላት አስተባባሪዎች፣ የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ዲንና ምክትል ዲኖች ተገኝተዋል፡፡

Read More »
The Minister Is answering questions live in zoomClick To join the live Meeting
+
en_USEN
Scroll to Top