Mols.gov.et

የሥራ እና ክህሎት ሚኒስቴር ሚኒስትር

ክብርት ወ/ሮ ሙፈሪሃት ካሚል

የህይወት ታሪክ

ክብርት ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል በ2014 ዓ.ም የተቋቋመው የኤፌዴሪ የሥራ እና ክህሎት ሚኒስቴር የመጀመሪያ ሚኒስትር ናቸው፡፡ ወደዚህ ሃላፊነት ከመምጣታቸው በፊትም በተመሳሳይ በ2011 ዓ.ም በሀገራችን እንደ አዲስ የተቋቋመውን የሰላም ሚኒስቴር የመጀመሪያዋ ሚኒስትር በመሆን አገልግለዋል፡፡ በቆታቸው ሚኒስቴር መቤቱን ከማደራጀት ጀምሮ ስድስት የሚሆኑ የሀገሪቱን የደህንነትና የፀጥታ ተቋማትን በብቃት መርተዋል፡፡ በሌላ በኩል 2002 እስከ 2004 ዓ.ም የሴቶች ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ሆነው ሰርተዋል፡፡ ክብርት ወ/ሮ ሙፈሪያት በተወካዮች ም/ቤት በተለያዩ ኃላፊነቶች ላይ ያገለገሉ ሲሆን ከሚያዚያ ዓ.ም 2010 እስከ ጥቅምት 2011 የመጀመሪያዋ ሴት አፈ ጉባኤ ሆነው ሰርተዋል፡፡ በሚኒስቴር ዴኤታ ማዕረግ የመንግስት ረዳት ተጠሪ እንዲሁም የትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ በመሆንም ምክር ቤቱን ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡ በተወካዮች ም/ቤት ከነበራቸው የሥራ ኃላፊነት ጎን ለጎን የመለስ ዜናዊ አመራር አካዳሚ ምክትል ፕሬዝደንት እንዲሁም የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማህበራዊ ጉዳይ አማካሪ በመሆን የተለያዩ ኃላፊነቶችን ሲወጡ ቆይተዋል፡፡ የትምህርት ዝግጅታቸውን በተመለከተ በትራንስፎርሜሽን አመራርና ለውጥ አስተዳደር ሁለተኛ ዲግሪያቸውን ከግሪንዊች ዩኒቨርሲቲ(ለንደን) እ.ኤ አ 2012 አግኝተዋል፡፡ ብራስልስ ከሚገኘው አንትሬፕ ዩኒቨርሲቲ በስርዓተ ፆታ ልማት የፖስት ግራጁየት ዲፕሎማ ትምህርታቸውን ተከታትለዋል፡፡ የመጀመሪያ ዲግሪቸውን በተመለከተም የአግሪካልቸራል ኤክስቴንሽን ትምህርትን በማጥናት ነበር ከሃሮማያ ዩኒቨርሲቲ ያገኙት፡፡ ክብርት ወ/ሮ ሙፈሪያት በፌዴራል መንግስት ወደሚገኙ ተቋማት በአመራርነት ከመምጣታቸው በፊት በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል የሴቶች ጉዳይ ቢሮ ምክትል ኃላፊ፣ በስልጤ ዞን የማህበሰብ ተሰትፎና ንቅናቄ ዘርፍ ኃላፊ እና በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ የህብረት ሥራ ፅ/ቤት ባለሙያ ሆነው ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በደቡብ ክልል ደህዴን ፅ/ቤት የማህበረሰብ ተሳትፎና ንቅናቄ ሃላፊና የክልሉ ፕሬዝደንት አማካሪ ሆነውም ሰርተዋል፡፡

amAM
Scroll to Top