Mols.gov.et

ዲጂታላይዜሽን ለቴክኒክና ሙያ ዘርፍ ልህቀት

ጥቅምት 2, 2024
ዲጂታላይዜሽን ለቴክኒክና ሙያ ዘርፍ ልህቀት በቴክኒክና ሙያ ዘርፍ የዲጂታላይዜሽን ትግበራ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ ተካሄደ፡፡ በመድረኩ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር፣ የቴክኒክና ሙያ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ በሬቻ(ዶ/ር) ሀገራችን በ2025 ዓ.ም ዲጂታል ኢኮኖሚን ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ ለማድረግ የሚስችል ዕቅድ መያዟን አስታውሰው የዕቅዱ ውጤታማነት እያንዳንዱ ዘርፍ ዲጂታላይዜሽንን ለማስፋፋት በሚያደረገው ጥረት ይወሰናል ብለዋል፡፡ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር በሁሉም ዘርፎች የሚያስፈፅማቸውን ተልዕኮዎች በራስ አቅም በለማው የዲጂታል ሥርዓት አማካኝነት እያስተገበረ እንደሚገኝ የገለፁት ክቡር ዶ/ር ተሻለ ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር በተለያዩ የፖሊቴክኒክ ኮሌጆች የዲጂታል መሰረተ ልማት ዝርጋታ፣ የይዘት ዝግጅትና የሰው ኃይል ልማት ሥራዎች በመሰራት ላይ እንደሚገኙ አስረድተዋል፡፡ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር በቅርቡ በመላ ሀገሪቱ ለሚገኙ የቴክኒክና ሙያ አሰልጣኝ መምህራን በሰጠው ስልጠና ላይ ዲጂታላይዜሽን አንዱ የትኩረት መስክ እንደነበር ያስታወሱት ክቡር ሚኒስትር ዴኤታው ክልሎችም አሰልጣኝ መምህራንንም ሆነ የቴክኒክና ሙያ ሰልጣኞችን ለዲጂታላይዜሽን ዘመን ዝግጁ ማድረግ እና ከፖሊቴክኒክ በታች ያሉ ኮሌጆችን በዲጂታላይዜሽን መሰረተ ልማት በማጠናከር ሥራ ላይ በንቃት መሳተፍ እንደሚኖርባቸው አሳስበዋል፡፡ በመድረኩ በቴክኒክና ሙያ ተቋማት ዲጂታላይዜሽን ለማስተግበር የተዘጋጀው ስትራቴጂ ቀርቦ በተሳታፊዎች ውይይት ተደርጎበታል፡፡
amAM
Scroll to Top