Mols.gov.et

የክህሎት እና የኢንዱስትሪ ፍላጎት አለመጣጣም …

March 22, 2024
የክህሎት እና የኢንዱስትሪ ፍላጎት አለመጣጣም(skills mismatch) በዘላቂነት የሚፈታ ሥራ በየአካባቢው በሚገኙ የሥራ ማስታወቂያ ሰሌዳዎች ሰብሰብ ብለው የሚጋብዛቸውን የሙያ መስክ የሚፈልጉ ወጣቶች መመልከት የዘወትር ተግባር ነው። አብዛኛው ስራ ፍለጋ የሚኳትኑት ታዲያ የኮሌጅ እና ዩንቨርስቲ ምሩቃን መሆናቸውም ይገለጻል። የስራ ማስታወቂያዎቹ ደግሞ ከማስታወቂያ ሰሌደዳዎች ባሻገርም በየስልክ እንጨቱ እና የመብራት ፖል ሳይቀር ተለጥፎ ቢታይም በአብዛኛው ክህሎት/ሙያ የሚጠይቅ መሆኑን እንመለከታለን። የዚህ ክፍተት ሁነኛ ምክንያት ደግሞ ተቋማት በተጨባጭ ኢንዱስትሪው የሚፈልገውን የሰው ሀይል እያፈሩ ባለመሆኑ እንደሆነም ይገለጻል። በተለይ ደግሞ ሰፊ የስራ እድል የመፍጠር አቅም ባለው የግብርና ዘርፍ ኢንዱስትሪው የሚፈልገውን በቂ ክህሎት ያላቸው ዜጎች ከማፍራት አኳያ ክፍተት መኖሩን ይጠቀሳል። ይንን ክፍተት የተገነዘበው የሥራና ክህሎት ሚኒስቴርም ከአለም ስራ ድርጅት(ILO proagro- promotion of decent work in agribusiness project) ጋር በመሆን ችግሩን ለመቅረፍ በግሉ ዘርፍ እና በመንግሥት አጋርነት የሚመራ የቴክኒክና ሙያ አስተዳደር ሥርዓት ለመዘርጋት ስራ እየሰራ ይገኛል። ይህንንም እውን ለማድረግ ከተለያዩ የመንግስት፣ አሰሪዎች እና ሰራተኞች እና ባለድርሻ አካላት የተውጣጣ የዘርፍ ክህሎት አካል ቴክኒካል ወርኪንግ ግሩፕ በማቋቋቋም፣ ለቡድን አባላቱ የአቅም ግንባታ እና የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና በአለም ስራ ድርጅት ድጋፍ በአዳማ ከተማ መስጠት ተጀምሯል። በመድረኩ የተገኙት የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የቴክኒክና ሙያ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ ዶ/ር ተሾመ ለማ ፤ ክህሎት ለአንድ ሀገር እድገት እና ኢንዱስትሪ ልማት እጅግ ወሳኝ መሆኑን ገልጸው ኢንዱስትሪው የሚፈልገውን ክህሎት ያላቸው ዜጎች ለማፍራት፣ ዘላቂ እና አስተማማኝ ኢኮኖሚያዊ እድገት ለማረጋገጥ ክህሎት የማይተካ ሚና ይጫወታል ብለዋለ። በሚኒስቴሩ የግብርና ሙያ ደረጃና ብቃት ምዘና ዴስክ ኃላፊ ዶ/ር ፍቃዱ አለማየሁ በበኩላቸው የቴክኒክ ቡድኑ ሁሉንም ባላድርሻ አካላት ባሳተፈ መንገድ የዘርፍ ክህሎት ልማትን የሚመራ አካል በማቋቋም የኢንዱስትሪውን የብቃት ፍላጎት የተላበሰ የሰው ሃይል በማፍራት፣ የሥልጠና አጠናቃቂዎች በሥራ ገበያው ውስጥ የሚኖራቸውን የሥራ እድል ለማሳደግ ትኩረት በመስጠት እንደሚሰራ ገልጸዋል። በመድረኩ በዘርፉ የተሻለ ተምክሮ ያላቸውን የጋና እና የደቡብ አፍሪካ ተሞክሮ ቀርቦ ውይይት እየተካሄደም ይገኛል።
Scroll to Top

The Ministry of Labor & Skills