Mols.gov.et

በየአካባቢው የሚገኙ የወጣት ማዕከላት እና የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ጣቢያዎችን…

May 16, 2024
በየአካባቢው የሚገኙ የወጣት ማዕከላት እና የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ጣቢያዎችን ሥራ በማቀናጀት የወጣቶች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ መስራት እንደሚገባ ተጠቆመ። በአዲስ አበባ ከተማ እድሳት የተደረገላቸውን የወጣት ማዕከላት ርክክብና የግብዓት ድጋፍ የተደረገላቸው የአንድ ማዕከላት አገልግሎት መስጫ ጣቢያዎች ሥራ የማስጀመሪያ ፕሮግራም ተካሂዷል። በርክክብ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የሥራ፣ ሥራ ሥምሪትና ገበያ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር አቶ ሰለሞን ሶካ እንደገለፁት፤ የወጣት ማዕከላት እንደሌሎች አንድ ማዕከላት ሥራ ፈላጊዎች የሚመዘገቡባቸው፣ የሥራ ገበያ መረጃ የሚያገኙባቸው እና የወጣቶች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጡባቸው ለማድረግ ማቀናጀት ይገባል ብለዋል። ሚኒስትር ዴኤታው በልደታ ክ/ከተማ በመገኘት በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ሙሉ እድሳት የተደረገለት የወረዳ 9 የወጣት ማዕከልን ቁልፍ ያስረከቡ ሲሆን በአዲሰ ከተማ፣ አራዳ እና በጉለሌ ክፍለ ከተሞች በመንግስት እና በዓለም ባንክ ድጋፍ እድሳት የተደረገላቸው እና ግብዓት የተሟላላቸው አራት የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ጣቢያዎች ሥራ አስጀምረዋል። የልደታ ወረዳ 09 ወጣት ማዕከልን እና አራቱን የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ጣቢያዎች በሞዴልነት በመውሰድ ሌሎች የወጣት ማዕከላት እና አንድ ማዕከላትን የማደስ እና በግብዓት የማጠናከር ሥራ እንዲስፋፋም ሚኒስትር ዴኤታው አሳስበዋል ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ አስፋው ለገሰ እና የከተማ አሰተዳደሩ የወጣቶች እና ስፖርት ቢሮ ሀላፊ አቶ በላይ ደጀን ለተደረገው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል።
en_USEN
Scroll to Top