Mols.gov.et

መንግስት የፈጠራ ስራዎችን በስፋት ጥቅም ላይ ለማዋል የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ ይቀጥላል

May 12, 2025
መንግስት የፈጠራ ስራዎችን በስፋት ጥቅም ላይ ለማዋል የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ ይቀጥላል መንግስት የክህሎት ልማትን ለማበልፀግና የፈጠራ ስራዎችን በስፋት ጥቅም ላይ ለማዋል ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ሀላፊና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ ገለጹ፡፡ ከሚያዚያ 27 ጀምሮ “ብሩህ አእምሮዎች በክህሎት የበቁ ዜጎች” በሚል መሪ ሐሳብ ሲካሄድ የቆየው አራተኛው ሀገር አቀፍ የክህሎት ውድድር ዛሬ ተጠናቋል፡፡ ውድድሩ በክህሎት፣ በቴክኖሎጂና ተግባራዊ ጥናትና ምርምር ዘርፎች ነው የተካሄደው። በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ሀላፊና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ በዚህ ወቅት እንደገለጹት ፤ የክህሎት ልማት የአገርን ተወዳዳሪነት ለመጨመር ወሳኝ ነው፡፡ መንግሥት የፈጠራ ሥራን ለመደገፍ በቁርጠኝነት እየሠራ መሆኑን ገልጸው፤ለአብነትም የሥራ እና ክህሎት ሚኒስቴርን ከማቋቋም ጀምሮ የቴክኒክና ሙያ ስልጠናን እያስፋፋ መሆኑን አንስተዋል፡፡ ክህሎት ያለው የሰው ሃይል ማፍራት ምርትና ምርታማነትንና የኢኮኖሚ እድገትን ለማፋጠን ብሎም አለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን ከፍ ለማድረግ ትልቅ ሚና እንዳለው ተናግረዋል። አገር አቀፍ የክህሎት ውድድር ኢትዮጵያ በዘርፉ ያስመዘገበቻቸውን ስኬቶች ያላቀ ቀሪዎቹን በብቃት መፈጸም የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የክህሎት ውድድሩ ማህበረሰቡ በሙያ ትምህርት ላይ ያለውን ግንዛቤ የሚያሳድግ መሆኑን አመልክተው፤ ወጣቶችን ለስልጠና የሚያነሳሳ እና የፈጠራ ስራዎች ደረጃቸውን ለማሻሻል የሚረዳ መሆኑን ገልጸዋል። የፈጠራ ስራዎች የኢትዮጵያን ብሩህ ተስፋና ብልፅግና እውን እንደሚያደርጉ ገልጸው፥የክህሎት ልማትና የፈጠራ ስራ ለማሳደግ የዘርፉ ተዋናይና የፈጠራ ባለቤቶች በትኩረትና በትስስር መስራት እንዳለባቸው ጠቁመዋል። መንግስት ለክህሎት ልማት እና የፈጠራ ሥራ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በበኩላቸው፥ ውድድሩ የሰልጣኞችን ክህሎት በተግባር በመፈተሽ ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን ለኢንተርፕራይዞች በማሸጋገር ምርትና ምርታማነታቸውን ለማሳደግ ያስችላል። አራተኛው ዙር አገር አቀፍ የክህሎት ውድድር የተሻሉ የፈጠራ ሥራዎች የታዩበት ነው ያሉት ሚኒስትሯ፤ በተለይም ጥራት ያላቸው እና ችግር ፈቺ የሆኑ ምርቶች በስፋት የተወዳደሩበት መሆኑንም ነው የገለጹት። ከአሸናፊዎቹ መካከል አዲስ አበባን ወክሎ በእንጨት ስራ ቴክኖሎጂ 1ኛ የወጣው ዳዊት ሃይለሚኪኤል በመሸለሙ መደሰቱን ገልጾ፥ ለዘርፉ የነበረው ፍቅርና ትጋት ለውጤት እንዳበቃው ተናግሯል። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ ከኦሮሚያ ክልል የመጣው ዮሃንስ ጥላሁን ተወዳዳሪ ሲሆን በምግብ ዝግጅት ተወዳድሮ 1ኛ መውጣቱ ገልፆ፤ የራሱ ጥረት የአስተማሪዎቹ እና የክልሉ ድጋፍ ለአሸናፊነቱ አስተዋፅኦ ማበርከታቸው አንስቷል። ከአማራ ክልል የመጣው አሸናፊ ከፈለኝ በበኩሉ የፊኒሺንገ ኮንስትራክሽን ተወዳድሮ 1ኛ የወጣ ሲሆን በቴክኒክና ሙያ ስልጠና የተገነባው አቅም ለዚህ ውጤት እንዳበቃው አንስቷል። ለሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳድሮች የምስክር ወረቀት የተበረከተላቸው ሲሆን፤ ለውድድሩ አሸናፊዎች የሜዳሊያ፣ የዋንጫና የገንዘብ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። በውድድሩ አንደኛ ደረጃ ይዘው ላጠናቀቁ ተወዳዳሪዎች የግማሽ ሚልየን ብር፣ የወርቅ ሜዳልያ እና የምስክር ወረቀት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። እንዲሁም ሁለተኛ ደረጃ ይዘው ላጠናቀቁ ተወዳዳሪዎች አራት መቶ ሺህ፣ የብር ሜዳልያና የምስክር ወረቀት ሽልማት የተበረከተላቸው ሲሆን፤ ሦስተኛ ደረጃ ይዘው ላጠናቀቁ ሦስት መቶ ሺህ፣ የነሃስ ሜዳሊያና እና የምስክር ወረቀት ተበርክቶላቸዋል። በውድድሩ የአሸናፊዎች አሸናፊ ዘርፍ አንደኛ አዲስ አበባ ከተማ አስዳደር ሁለተኛ ኦሮሚያ ክልል እና ሦስተኛ አማራ ክልል ሆነው አጠናቀዋል። ዘገባው የኢዜአ ነው።
tigTIG
Scroll to Top